Saturday, June 1, 2013

የኢትዮጵያ ግድብ የጦርነት አዋጅ ነው አል-ጋማ አል-ኢስላሚያ የግብፅ ሚኒስትሮች ካቢኔ ረቡዕ በአስቸኳይ ተሰበሰበ...

 የኢትዮጵያ ግድብ  የጦርነት አዋጅ ነው  አል-ጋማ አል-ኢስላሚያ   የግብፅ ሚኒስትሮች ካቢኔ ረቡዕ በአስቸኳይ ተሰበሰበ...
የኢትዮጵያ የሕዳሴው ግድብ ግንባታና የጥቁር አባይ ወንዝ ውሃን አቅጣጫ የማስቀየር ተግባር ‹‹በግብፅ ላይ ጦርነት እንደማወጅ ነው›› ሲሉ ሼክ እብዱል አክሀር ሙሐመድ ተናገሩ፡፡ የአል-ጋማ አል-ኢስላሚያ አመራር ‹‹አል-አረቢያ›› ከተሰኘው የሳተላይት ቴሌቪዥን ጋር ቃለ- ምልልስ ባደረጉበት ወቅት ይህን ያሉት ኢትዮጵያ ባለፈው ማክሰኞ ግንቦት 20 ቀን 2005 የግድቡ ስራ አካል የሆነውን የወንዙን ፍሰት አቅጣጫ ማስቀየር ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ነው፡፡ ሼህ ሙሐመድ ድርጊቱ ‹‹የግብፅን የውሃ አቅርቦት የሚቀንስና በብሔራዊ ደህንነቱን የሚያበላሽ ነው›› ብለውታል፡፡ ጨምረውም ‹‹በእኛ ላይ ጦርነት የሚያንዣብብ ከሆነ ለመዋጋት ዝግጁ ነን፡፡ ሁሉንም ጥንካሬያችንን ተጠቅመን ክብራችንን እናስጠብቃለን›› ሲሉም ተናግረዋል፡፡ ይሁንና ከዚህ በፊት ዲፕሎማሲያዊ ስምምነቶች ማድረግ እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል፡፡
አሕራም የተሰኘው የግብፅ ጋዜጣ በኦን ላይን ዕትሙ ከሰሞኑ ባሠፈረው አዲስ መረጃ መሠረት፣ ግብፅ ከአባይ ወንዝ አሁን ከምታገኘው የበለጠ የውሃ ኮታ እንዲኖራት ትፈልጋለች፡፡ ጋዜጣው የአገሪቱን ብሔራዊ የፕላኒንግ ኢኒስቲትዮት ጠቅሶ ባቀረበው ዘገባ በአሁኑ ወቅት ግብፅ ከአባይ ወንዝ በዓመት እያገኘችው ያለው ውሃ 55 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ቢሆንም (እ.ኤ.አ) በ2050 ግን ተጨማሪ 21 ቢሊዮን ኪዩብክ ሜትር ማግኘት ይኖርባታል፡ ፡ ምክንያቱም በተጠቀሰው ዓመት የግብፅ ሕዝብ ብዛት 150 ሚሊዮን እንደሚደርስ ስለሚገመት 55 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትሩ ብቻ እንደማይበቃው በጋዜጣው ተመልክቷል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ማክሰኞ ዕለት ይፋ የሆነው የወንዙ አቅጣጫ ማስቀየር ስነ-ሥርዓት በግብፅና በሱዳን መሐከል ድንጋጤ ሳይፈጥር እንዳልቀረ እየተሰራጩ ያሉት ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡ የግብፅ መንግስታዊ የዜና አውታር የሆነው መና እንዳመለከተው በዚሁ ዙሪያ ለመነጋገር የሱዳኑ የመስኖ ሚኒስትር ኦሳማ አብዱላህ አል- ሀሰን ረቡዕ ዕለት ካይሮ ገብተዋል፡ ፡ በተጨማሪም በኢትዮጵያ የግብፅ አምባሳደር ሙሐመድ ኢድሪስ በዚሁ ዕለት ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚ/ር ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር እንዲመካከሩ መደረጉን የዜና አውታሩ አስረድቷል፡፡
በግብፅ፣ ሱዳንና ኢትዮጵያ ባለሙያዎች እየተዘጋጀ ያለውንና ፕሮጀክቱ ስለሚያመጣው ተፅእኖ የሚገመግመውን የሶስትዮሽ ሪፖርት ውጤት ካይሮ እየጠበቀች መሆኑን የዜና ተቋሙ ጠቁሞ የካይሮ ባለሥልጣናት የኢትዮጵያን እርምጃ ግብፅን እንደማይጐዳ ግምት ማሳደራቸውን አመልክቷል፡፡ የፕሬዝዳንት መሐመድ ሙርሲ ዋና አማካሪ ኢሳም ሀዳድ ‹‹ግንባታው በግብፅም ሆነ በአባይ ወንዝ ውሃ ላይ የሚያመጣው ቀጥተኛ ተፅእኖ የለም›› ሲሉ እንደተናገሩም አስቀምጧል፡፡
ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ እርምጃ ስጋት የፈጠረባቸው የግብፅ ባለስልጣናትም አሉ፡፡ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ እንደዘገበው ማክሰኞ ዕለት ይፋ በሆነው ድርጊት ዙርያ በጠቅላይ ሚኒስትር ሀሺም ቋደል የሚመራው ካቢኔ ረቡዕ ዕለት ስብሰባ ተቀምጦ አውርቶበታል፡፡
የካርቱም ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ረቡዕ ዕለት በሰጠው መግለጫ ደግሞ በሱዳን፣ ግብፅና ኢትዮጵያ መካከል ስምምነትና ምክክር በመኖሩ የተነሳ በፕሮጀክቱ ሱዳን እንደማትጐዳ ገልጿል፡፡
‹‹ሱዳን ከሁለቱ አገራት (ግብፅና ኢትዮጵያ) ጋር የአባይ ውሃን ክፍፍል በተመለከተም የጋራ ተጠቃሚነትን ያማከለ መጋራት እንዲኖር ለማስቻል የፈፀመችውን የትብብር ስምምነት ታከብራለች›› ብሏል፡፡ የውጭ ጉዳይ መ/ቤቱ መግለጫ፡፡
በተያያዘ ዜና የግብፅ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በኢትዮጵያ የሚገኙትን የግብፅ አምባሳር ጠርቶ ማነጋገሩን አሕራም ኦን ላይ ዘግቧል፡፡
ግድቡ የሚያስከትለውን ጉዳት በተመለከተ የማጣራት ስራ እያከናወነ ያለው በሶስቱ አገራት ባለሙያዎች የተውጣጣው ኮሚቴ የመጨረሻ ሪፖርቱን በዚህ ሳምንት ይፋ እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ባሳለፍነው ሣምንት ግንቦት 20ን ምክንያት በማድረግ በአባይ ወንዝ ላይ የተደረገው የማስቀየስ ሥራ ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ በይፋ መበሠሩ የግድቡን ሥራ ወደ አንድ ደረጃ እንዳደረሰው የተገለፀ ሲሆን፡፡ታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ከተጀመረ ጀምሮ አጠቃላይ ግንባታውን በ2005 በጀት ዓመት መጨረሻ 26 በመቶ ለማድረስ የታቀደ ሲሆን እስካሁን ባለው ሁኔታ ፕሮጀክቱ 21 በመቶ አፈፃፀም ላይ ደርሷል፡፡
በግድብ ግንባታ ስራ ወንዝ መቀልበስ ወይም River Diversion በጣም ወሳኝ ከሆኑ ሥራዎች አንዱ ሲሆን ይህንን ለማሳካት ዲዛይን ለውጥ በማድረግ ክረምት ከበጋ ግድቡ አካባቢ መስራት በሚያስችል ሁኔታ የተሠራ ሲሆን የማስቀየሻ ካናሉ እስከ 14700 m3/s ውሃ የማስተላለፍ አቅም ይኖረዋል ብለዋል የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፕሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ምህረት ደበበ፡፡
ከግድቡ ስራ ጋር በተያያዘ እስከአሁን በአጠቃላይ የቁፋሮ ክንውን መጠኑ ከ6 ሚሊዮን ሜትር ኩብ በላይ የደረሰ ሲሆን በግራና በቀኝ የኃይል ማመንጫ ቤት ቁፋሮም እስከ 1.7 ሚሊዮን ሜ.ኩብ ደርሷል፡፡
ከ G e o t e c h n i c a l investigation አንፃር አንድ የሚቀረው ሥራ የወንዝ መሄጃ በነበረው አካባቢ በቀጣይነት የሚሠራ ሥራ ሲሆን አካባቢው ከውሃ ነፃ በተደረገ ማግስት ጀምሮ የሚሠራ ሥራ ይሆናል፡፡
ሌላው የወንዝ የመቀልበሻ አካል የሆነው ከግድቡ በስተግራ በኩል በአራት ድፍን ትቦዎች (culverts) የሚገነባበት ቦታ ለሁለተኛ ጊዜ የወንዙን አቅጣጫ ማስቀየር የሚችል ሲሆን የዚህ ቁፋሮ ስራ በተቀላጠፈ ሁኔታ እይተሠራ ሲሆን የብረታብረት ቱቦዎች ሥራም በብረታ ብረትና ኢነጅነሪንግ ኮርፖሬሽን እንደሚሠራ ጠቁመዋል፡፡
ከዚህ የኃይል ማመንጫ የሚገኘውን ኃይል ወደተጠቃሚው ለማድረስ የሚያስፈልጉ በሶስት አቅጣጫ የሚሄዱ 500 ኪ.ቮ አቅም ያላቸው የማስተላለፊያና የማከፋፈያ ጣቢያዎች ጥናት፣ ዲዛይን ተዘጋጅቶ የመጀመሪያው ምዕራፍ ከታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ዴዴሣ ሆለታ ኮንትራት ተፈርሞ ወደ ግንባታ የተገባ ሲሆን በተያዘለት ጊዜም ይጠናቀቃል ተብሏል፡፡
ይህ ስራ የአገር አቅማችንን ከፍ ያደረገልን ሲሆን ከዚህ ቀደም እስከ 400 ኪ.ቮ የምናካሂደውን የጥናት፣ የዲዛይንና የኮንትራት ሠነድ ማዘጋጀት አቅማችንን ወደ 500 ኪ.ቮ ከፍ ማድረግ አስችሎናል ብለዋል፡፡ እንደ አቶ ምህረት ገለፃ ፡፡
ኃላፊው አያይዘውም በመንግሥት በኩል በቀናነነት ለተወሰደው ይሄው ግልፅነት ያለው እርምጃ ሌላ ትርጉም ተሰጥቶት በኤክስፐርቶች አማካኝነት በግንባታው ሂደት ላይ ተፅእኖ የማሳደር የተሳሳተ አመለካከትን በንቃት መከታተል እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር የሆኑት አቶ አለማየሁ ተገኑ በበኩላቸው ከአለም ታላላቅ ወንዞች ተርታ የሚሰለፈው ታላቁ ወንዝ ዓባይ ለናይል ተፋሰስ 86 በመቶ የሚሆነውን የውሃ ድርሻ ቢያበርክትም እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ግን ሀገራችንና ህዝቦቿ ይህንን መሠል የተፈጥሮ ሀብቶቻችንን መጠቀም ተስኗቸው የድርቅ ተጋላጭ ሆነው አስከፊ ህይወትን እንዲኖሩ ተገደው ቆይተዋል ካሉ በኋላ የግድቡ ግንባታ በታችኛው የተፋሰሱ አገራት ላይ ጉልህ ጉዳት እንደማያደርስ ይልቁኑም ለሶስቱም አገራት ማለትም ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳን የሚሰጠውን ጥቅም የጥናት ሰነዶችን በመመርመር እንዲያረጋግጥ የተቋቋመው የግድቡ የአለም አቀፍ ባለሙያዎች ቡድን ሥራውን በማጠናቀቅ ላይ ይገኛል፡፡ ቡድኑ የሚያወጣው ሪፖርት ሁሉም የተስማሙበት የጋራ ሪፖርት በአገራቱ መካከል መተማመንና ትብብርን እንደሚያጠናክር ገልፀዋል፡፡

No comments:

Post a Comment