Tuesday, June 11, 2013

ኢትዮጵያ በቀረርቶ ተደናግጣ ለሰከንድ የግድብ ግንባታዋን አታቆምም – የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር

969694_588045714550673_1440883208_n
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታን አስመልክቶ የግብፅ አንዳንድ ባለስልጣናት ፣ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችና የተለያዩ ማህበራት ሀላፊዎች ሲያካሂዱ የከረሙትን አፍራሽ ፕሮፖጋንዳ በተመከለተ ዛሬ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጫ ሰጥቷል ።
ሚኒስቴሩ በመግለጫው ኢትዮጵያ በጉዳዩ ላይ ያላትን ገንቢ አቋም ገልፃ ነገር ግን በግብፅ በኩል የአገሪቱን አቋም በኢትዮጵያ የግብፅ አምባሳደርን ከአንዴም ሁለት ጊዜ ጠርታ መጠየቋንና ለግብፅ መንግስት ጥያቄ ማቅረቧን ያስታውሳል ።
ኢትዮጵያ ከምንም በላይ ለትብብር ፣ ለወዳጅነትና ለጋራ ጥቅም ያላትንም ፅኑ እምነት በወቅቱ ግልፅ አድርጋለች ያለው መግለጫው ፥ ይህ በእንዲህ እንዳለ ትናንት ብሄራዊ የናይል ጉባኤ በተሰኘው ስብሰባ ላይ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፣ ሚኒስትሮችና ሌሎችም በተገኙበት ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አስመልክቶ አፍራሽ መልዕክቶች ሲተላለፉ መቆየታቸውን አንስቷል ።

የህዳሴ ግድብ በግብፅ ላይ አደጋ በመደቀኑ በኢትዮጵያ ላይ በተለያዩ መንገዶች ተፅእኖ የማሳረፍና የግድቡን ግንባታ እንድታቆም የማድረግ እንቅስቃሴ ስለ ማድረግ የሚገልፁ ፣ በአጠቃላይ ከኢትዮጵያ ፍላጎትና አድራጎት ውጪ እንዲሁም የህዳሴ ግድቡን እንዲያጠና ግብፅ ጭምር ያለችበት የዓለም አቀፍ የባለሙያዎች ቡድን ያቀረበውን ሪፖርት ጭምር የሚያጣጥሉ ፀብ ጫሪ አስተያየቶች በመድረኩ ሲስተናገዱ መስተዋላቸውን ነው መግለጫው የጠቆመው ።
በዚህ ረገድ በግብፅም ሆነ በሌላ ማንኛውም ወገን የሚቀርብ የግድቡን ግንባታ የማዘግየት ወይም ከነአካቴው የማቋረጥ ነገር ፈፅሞ ተቀባይነት እንደማይኖረው ገልጿል ።
በህዳሴው ግድብ ሽፋን የውስጥ ችግርን ለማቃለል የሚደረገው ጥረት የግብፅን ዘላቂ ጥቅም አይጠብቅምም ብሏል ።
ጦርነትና ሌሎች አፍራሽ ስልቶችን ስለመጠቀም የሚቀርቡት ሀሳቦች ያረጁና ያፈጁ ፣ የ21ኛውን ክፍለ ዘመን አስተሳሰብ የማይሸከሙ ፣ ጤናማ ያልሆኑ አስተሳሰቦች እንደሆኑና ኢትዮጵያ በዚህ ቀረርቶ ተደናግጣ ግንባታውን ለሰኮንድም እንደማታቆም አረጋግጧል ።
የግብፅ ወገንም ከዚህ አፍራሽ ድርጊት ተቆጥቦ ለሁለቱ አገራት ግንኙነት መጠናከር የበኩሉን ጥረት እንዲያደርግ ሚኒስቴሩ አሳስቧል ።
በዚህ አጋጣሚ የሱዳን ማስታወቂያ ሚኒስትር የህዳሴ ግድቡን ግንባታ ጠቀሜታ አስመልክተው ያሰሙት ሀሳብ ገንቢ በመሆኑ አመስግኗል ፤ ሌሎች ከዚህ የሚቀስሙት ትምህርት እንዳለም አስታውቋል ።
በሌላ በኩል ይህ ግድብ ግብፅን ጭምር የሚጠቅም መሆኑን በማሳሰብ ኢትዮጵያ ከግብፅ ጋር በወዳጅነትና በትብብር ለመስራት ፅኑ ፍላጎት እንዳላት ገልጿል ።
አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 4 ፣ 2005 (ኤፍ ቢ ሲ)

No comments:

Post a Comment