Saturday, August 24, 2013

የምንፈልገውን ለውጥ ለማምጣት የሚያስችሉን ነገሮች ምንድን ናቸው?

ዛሬ ኢትዮጵያ አገራችን ከምትገኝበት ልዩ ልዩ ማህበራዊ፣ የህልውና ቀውስና ችግር፣ ለማውጣትና የተሻለ ሥርዓተ ማህበር ለመመስረት ምን መደረግ አለበት የሚለውን ጥያቄ በርከታ የወገን መከራና ስቃይ የሚያሳስባቸው ኢትዮጵያውያን ሁሉ የሚጠይቁት የወቅቱ ተደጋጋሚ ጥያቄ ነው።ለጥያቄዎቹ መልስ ይሆን ዘንድ ብዙ ታሪካዊና ወቅታዊ የፖለቲካ ትንታኔዎች ተሰጥቷል ፣ብዙም ተጽፏል ፣ብዙም ተነግሯል፣ ሆኖም ግን አገራዊና ማህበራዊ ችግራችን ከመቸውም ግዜ የበለጠ እየከፋና እየባሰ መጣ እንጂ
ለመሰረታዊ የለውጥ መፍትሄ የሚያበቃን እውነተኛና ተግባራዊ መልስ አልተገኘም ። በተጨባጭ ወቅቱ የሚጠይቀውን አውንታዊ ምላሽ አልሰጠንም።
በተገቢው ግዜ ተገቢውን መልስ በመስጠት የገጠመንን ውስብስብ ችግር በጥራት አውቀን ለድል አሸጋጋሪ የሆኑ መንገዶችን መፍጠር ለግዜው አልቻልንም። ስለዚህ ጥያቄው ለምን አልቻልንም ነው?እንድንችልስ ምን መደረግ ይኖርበታል? ለዚህ ጥያቄም ሆነ
ለሌሎቹ አንድ ወጥና ለሁሉም ግልጽ የሆነ መልስ ባይኖርም ፣ ወሳኝ የሆኑትን የችግሮች ባህርያትና መንስኤዎች በትክክል መርምሮና ለይቶ ማወቅ ፣ለጥያቄያችን መልስና ለምንሻው መፍትሄ አስፈላጊ የመጀመርያ የተግባር እርምጃ ነው። የዚህ አጭር ጽሑፍ ዋና ዓላማም አንዳንድ ወሳኝ ጥያቄዎችን በማንሳት አሁን ከምንገኝበት የአስተሳሰብና የምግባር አዙሪት ውስጥ መንጥቆ ሊያወጣን የሚያስችል አቅም ገንቢ፣ መፍትሄ አዘልና ውጤታማ ሃሳቦችን ለመጠቆምና ለማመላከት ብሎም በትግላችን ሂደት ላይ
እምርታዊ አስተሳሰብን ለመፍጠር እንዲያስችለን ነው። እንደሚታወቀው ሁሉ ለማንኛውም ችግር መፍትሄው በከፊል የችግሩን ምንነት በትክክል ማወቅና
መገንዘብ ላይ የተመሰረተ ነው።ችግሩን በቅጡ ማወቅ ማለት መፍትሄውን ፍሬያማ ከማድረግ ጋር የተያያዘና የተሳሰረ ነው። ስለ ችግራችን መጠንና ዓይነት ያለን ዕውቀትና ግንዛቤ በተግባር ካልተተረጎመ ፣ ችግርን በተናጠል መዘርዘርና መተንተን ብቻ ከጥቅሙ ጉዳቱ የሚያመዝንበት ሁኔታ ይፈጠራል፣ ተፈጥሯልም። ችግራችንን ማወቅና መገንዘብ ላይ ብቻ ከተወሰንን ወደ ተፈላጊውና ቀጣይ ተግባራት እንዳንሸጋገር ያደርጋል። የትግላችንም ሂደት መፍትሄ ሳይሆን ችግርና ደካማነትን ማዕከል እንዲያደርግ
ያደርገዋል።አንደኛው የገባንበት የአዙሪት ምክንያት የሆነው ይሄው አካሄድ ነው።መፍትሄ ፈላጊውን ኃይል ባለበት እንዲረግጥ ሲያደርገው፣ በአንጻሩ ግን ማህበራዊና አገራዊ ችግሮቻችን መጠናቸውን አልፈው የማይጠገኑበትና የማንቀለብስበት ደረጃ ይደርሱና የማንፈልገውን ዘለቄታዊ ጥፋትን እንዲከሰት
ይሆናል ።ለዚህም ነው አስፈላጊውን ተግባር በተገቢው ግዜ ማካሄድ የሚያስፈልገው።ማንኛውም የህይወት ጉዳይ በወቅቱ ካልተከናወነ ፣ችግር ተሸካሚዎች እንድንሆን ያደርገናል እንጂ፣ መፍትሄ አፍላቂ የለውጥ ባለቤት የሆነ ሕዝብ አያረገንም ፣ ይህ ባህሪ ደግሞ በትግላችን ሂደት ላይ ከፍተኛ ችግር አስከትሏል። ላለንበት ሁኔታ የሚመጥን የተግባር መልስ መስጠት ካልቻልንና የተሸናፊነት ፣የተጎጂነትና
የተበዳይነት ስነ ልቦናዊ መንፈስ እየዳበረ ከመጣ ፣ችግርን የመፍታት ችሎታችንና ኃይላችን ይዳከማል። የገጠመንን አገራዊ ማህበራዊ ቀውስ ለመውጣት የችግሮቻችን ስረ መሰረታና መንስኤ በትክክል መገንዘብ ፣ምን መደረግ አለበት ለሚለው ጥያቄ ተገቢ መልስና አቅጣጫ ሊሰጥ ይችላል ብየ አምናለሁ።በተለይም ችግርን ከመፍትሄው ሳንነጥል አዎንታዊ ሂደት የሚያስከትሉ ጥያቄዎችን በማንሳት እስከዛሬ
ከተጓዝንባቸው መንገዶችና አስተሳሰቦች የተለዩ ሂደቶችን ለይተን እንድናውቅ ይረዳናል። የተግባራዊ እንቅስቃሴዎችንም ቅደም ተከተልንም ለማስያዝና ግዜን በአግባቡ ለመጠቀም ያስችለናል። በተጨማሪም አሁን ላለንበት ማህበራዊ ቀውስ ለምንና እንዴት ለዚህ ያበቃን የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ የምንጠቀምበት የአመለካከት መነጽር ሆነ የምንመራበት ርዕዮት በምናገኘው መልስና መፍትሄ ላይ ተጽዕኖ ስለሚያደርግ የምናይበት አንጻራዊ መነጽር ምን መሆን አለበት የሚለውንም ጥያቄም ማንሳት ተገቢ ነው። ካለንበት አስጊ ሁኔታ ለመውጣት የምንጠይቃቸው ጥያቄዎች ሰፊ ሁለገብና የተሳሰሩ ናቸው። የችግሮቻችን ዋና ገጽታና መገለጫቸውስ ምንድን ናቸው: ምን መደረግ አለበት የሚለውን አጠቃላይና አመላካች ጥያቄን ለመመለስ በ ቅድሚያ መነሻና መንደርደሪያ ይሆነን ዘንድ የአገራችንን ነባራዊና ወቅታዊ ሁኔታውችን ባጭሩ መዳሰሱ አስፈላጊ ነው። ኢትዮጵያ ዛሬ ኢትዮጵያ ከመቼውም ግዜ በበለጠ የከፋ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊ ቀውስና አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ መገኘትዋ ብቻ ሳይሆን ፣ እንደ አገር በዘላቂ ህልውናዋ ላይ ፣ እንደ ህዝብ በነጻነቱና በአንድነቱ ላይ
የተነጣጠረው ጥቃት አስጊና አሳሳቢ መስቀለኛ ቦታ ላይ እንድትገኝ አድርጓታል። ለዚህም አስከፊ ማህበራዊ ሁኔታ የዳረጋት በቅድሚያ ወያኔ የትግሬ ነጻ አውጪ ግንባር ሲሆን ፣በዓለም ዙሪያ የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶችና ተቀናቃኝ ጸረ አንድነት ኃይሎች ትብብርና ድጋፍ ጭምር ነው።
የመጀመርያውና ዋነኛው የወያኔ ፀረ ኢትዮጵያዊነት ስሜት በተግባር የተገለጠው ግዛታዊ ሉዓላዊነትዋን የገፈፈ፣ዳር ድንበርዋን ያፈረሰ፣ብሎም የህዝብዋን አንድነት የሚያናጋ ሕገ መንግስት በመደንገግ ነው፤ እንዲሁም የጎሳዎች ጥርቅም የሚኖሩባት መልክዓ ምድር ነች በማለት አገራት ሲፈጠሩ የመጀመርያ ከነበሩት አንድዋ ኢትዮጲያን ህልውናዋን የሚክድና ፅንፈኛና በጥፋት መንፈስ የታነፀ የሃሰት አስተሳሰብን
መሳሪያ በማድረግ ነው። በዓለም ላይ የአንድ አገር ግዛታዊ ሉዓላዊነትን ማክበርና ማስከበር መንግስትን መንግስት ከሚያደርጉት አንደኛውና ዋንኛ ባህሪ ነው ። ሆኖም ወያኔ የትግሬ ነፃ አውጭ ግንባር አገዛዝን ልዩ የሚያደርገው፣ በጎሳዊ ስሜትና አስተሳሰብ በመታሰሩ እራሱን የካደ ፀረ ኢትዮጵያ ስነልቦና የሰረፀበት ድርጅትና የፖለቲካ ማህበረሰብ መሆኑ ነው። ይሄን የወያኔን ባህሪ አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ሁሉ
ጠንቅቀው ውስጠ ሚስጥሩንና አሰራሩን ሊያውቁ ይገባል፣ ይህን ማድረግም ለገጠመን ፈተና ተመጣጣኝ ኃይልና ዝግጅት በሃሳብም በተግባርም እንዲኖር ይረዳል። ይህ የወያኔ የትግሬ ነፃ አውጭ ድርጅት ጎሳዊ የክልል አገዛዝ የአገራችን ኢትዮጵያን ዳርድንበር ፣ ግዛታዊ ሉዓላዊነት በመድፈር ብቻ ሳይወሰን አገራዊ ብሄራዊ ህልውናዋን ለማናጋትና ለማፍረስ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል። ለሕይወት መሰረት ለዓይን ውበት የሆነው የተፈጥሮ ፣የባህል፣ የሃይማኖት፣ የቋንቋና የኑሮ ዘይቤ ዓይነቶችና ገጽታዎች ልዩ
ልዩ የጋራ መገለጫ ጸጋዎች ናቸው እንጂ የፖለቲካ የስልጣን መወጣጫ መሳሪያዎች አይደሉም። ወያኔና መሰሎቹ የፖለቲካ መሰረተ ሃሳብ የሚያጠነጥነው ግን እነዚህን የተፈጥሮ ጸጋዎች የመከፋፈያና የስልጣን መፈናጠጫ መሳርያ በማድረግ በሕዝብ መካከል የሃሰትና የጠላትነትን መንፈስ የሚያሰራጭ የጸረ አንድነት ፖለቲካ መርሆን በአገር ላይ በማራመድ ነው። ለዘመናት በታሪካዊ ሂደት፣ በተፈጥሮ በባህል ፣
በሚታይና በማይታየው ረቂቅ የጋራ ምንነትና ማንነት የተሳሰረ ሕዝብ መሆኑን በመካድና በመከፋፈል ለባርነት ምቹ እንዲሆን ያደርገዋል።ወያኔ የትግሬ ነፃ አውጭ ግንባር ላለፉት ሃያ ሁለት ዓመታት የኢትዮጵያ ሕዝብ ታሪካዊ ስነልቦናዊና አካላዊ አንድነቱን እንዲክድና እንዲጠራጠር ብሎም በማናነቱ ላይ ያለውን አመለካከት እንዲዛባ ከፍተኛ ጥረት አድርጓል።
ዛሬ አገራችን በወያኔ የትግሬ ነፃ አውጭ አገዛዝ ብሔራዊ ሕልውናንና አንድነትን በማናጋት ሕዝባችንን ለዘመናዊ ቅኝ ተገዥነት ዳርጎታል ። በሽያጭም ሆነ በንግድ መልክ ለባዕዳን የሚቸረቸረው የኢትዮጵያ ገበሬ የእርሻ መሬት የዘመናችን ልዩ የቅኝ ግዛት ስልት መሆኑ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያነጋገረ አሳሳቢና አሳዛኝ ሃቅ ነው። የወያኔ የትግሬ ነፃ አውጭ ግምባር አገዛዝ ፀረ ኢትዮጵያዊነቱ ሌላው መገለጫው ይህ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ከማስጠበቅና ከማስከበር ይልቅ ለባዕዳን አገሮች ሃብታም ነጋዴዎችና
መንግስታት አድልዎ በማድረግ፣ በተለይም የአገርን ብሔራዊ ሃብት ሻጭና ደላላም በመሆን የአገር ክህደትን መፈጸሙ ነው። ይህም ሁኔታ ቀስ በቀስ በስውርም ሆነ በቀጥተኛ መንገድ ኢትዮጵያውያንን በአገራቸው ውስጥ ሁለተኛና ዝቅተኛ ዜጎች እንዲሆኑ እያረጋቸው ነው። ዛሬ በአገራችን ውስጥ በኢኮኖሚና በፖለቲካ መስክ ብቻ ሳይሆን በስነ አዕምሮ፣ በባህል፣ በሃይማኖት ፣በቋንቋ ወዘተ ላይ የዝቅተኝነት ቦታ በመያዝ፣ የቅኝ ተገዥነትን ባህርያትን በስፋት እየዳበረና እየተንጸባረቀ ይታያል።
በርካታ የባዕድ መንግስታትና ነጋዴዎች በአገራቸው ውስጥ ያላገኙትን ሃብት ምቾትና አልፎም የበላይነትን በኢትዮጵያ ውስጥ እንዲያገኙ፣የወያኔ አገዛዝ እያመቻቸላቸው ይገኛል። ኢትዮጵያውያን በአገራቸው የተነፈጉትን የድሎት ሕይወት ባዕዳን እየተጎናጸፉ ነው። የወያኔ ክልላዊ የጎሳ አገዛዝ ልዩና አደገኛ የሚያደርገው ሌላው ባህሪ ይህ አገራዊ ብሔራዊ ስሜት በጎሳዊነት ስሜት የተዋጠ መሆኑ ነው። ብሄራዊ አስተሳሰባቸው፣በጥላቻና በዝቅተኝነት ስሜት የተበከለና የተመረዘ ስነ ልቦና ላይ የታነጸ በመሆኑ አገራችንን ለዘመናዊ ባርነትና ቅኝ ተገዥነት ዳርጓታል። በተፈጥሮ ጸጋዋ ሃብታምዋ አገራችን የሌሎች አገር ሕዝብን ስትመግብን ስታበለጽግ ፣የራሳችን ሕዝብ ግን በድህነትና በረሃብ በመማቀቅ በዓለም የመጀመርያውን የድህነት ቦታ ይዛለች። በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ሴቶች ለዘመናዊ ባርነት፣ ሕጻናንት በማደጎ ስም፣ወጣቶችን በፖለቲካ ጭቆናና ድህነትን ለመሸሽ በሚል ምክንያት ወደ ውጭ አገር በገፍ በማጋዝ ለተለያየ የግፍ ሰለባና ለዓለማቀፍ ኢሰብዓዊ ወንጀል ተጋልጠው ይገኛሉ ። በአገሩ ውስጥ አርሶ መኖር እንዳይችል ከመሬቱ የተፈናቀለው ገበሬ ስደትንና ባርነትን እንደ አማራጭ እንዲቀበል ተደርጓል፣ አልፎም በረቀቀ ዘዴ በቅርቡ በዐማራው ማህበረሰብ ላይ እንደታየው፣የህዝብን ቁጥር ለመቀነስ ዘርን በማምከን ኢሰብዓዊ ወንጀል ይፈጽማል።ኢትዮጵያዊ ሃይማኖቶችና ባህሎች በባእዳን አስተሳሰብና
አመለካከት እየተተኩና እየተበከሉ በመምጣት ላይ ናቸው። አንድ ሕዝብ ሆነ ማህበረሰብ አካላዊ፣ስነልቦናዊ፣መንፈሳዊና ባህላዊ የህልውና ሉዓላዊነቱን ማጣት ከትውልድ ትውልድ ለሚተላለፍ ለኢኮኖሚም ሆነ ለፖለቲካ የበታችነት ይዳርገዋል።
ኢትዮጵያ ዛሬ ይህን በመሰለ የጭቆና ቀምበር ውስጥ ብትወድቅም የሰው ልጅ መገኛ ፣የስልጣኔ ምንጭ ታላቅና ክቡር አገር እንደነበረች አይካድም። ክብሯንና ነጻነትዋን ሳታስደፍር ለብዙ ሺህ ዘመናት ኖራለች።አንደኛው የሚደነቀው የስልጣኔ ምልክትዋም ይህ የነጻነት ወዳድነትዋና ባለቤትነትዋ ነበር።
ይህም አኩሪ ብሄራዊ ጸጋ በዋዛ የተጎናጸፈችው ሳይሆን በህዝቧ የመሰረታዊ የባህሪ ማለትም ጀግንነት ፣ ራስን ማወቅ በመሳሰሉት የማንነት ውጤት ነበር። የጥንት ኢትዮጵያውያን ታሪካዊም ሆነ ወቅታዊ ኑሮ የሚፈጥራቸውን ማህበራዊ ውጥንቅጥና ችግሮችን የሚወጡት ራሳቸውን ማዕከል ባደረገ መንገድና ዘዴ በመጠቀም መፍታት የሚችሉ ሊቆችና መሪዎች ስለነበሩ ነው። ማንነታቸውና ምንነታቸው ከራስ የውስጥ
ባህሪና ስነምግባር ጋር እንደዛሬው ትውልድ በአሉታዊ መልክ የተቃረነና የተበረዘ አልነበረም።
ለእንቅስቃሴያችን ታላቁን የዓላማችን ግብ መምታት ማለትም ኢትዮጵያ አገራችን ካለችበት የባርነት ቀምበር ተላቃ ፍትህና ርትዕ የሰፈነባት ፣አንድነትዋና ብሄራዊ ህልውናዋ የተከበረባት አገር ለማድረግና ለዚህም የሚያበቃን መንግስታዊ ስርዓት ለመመስረት ነው። ታድያ ይህንን በተግባር ዕውን ለማድረግ፣ ኢትዮጵያንና ሕዝቧን የሚወዱ ሁሉ ምን ማድረግ ይኖርብናል?ከብዙ በጥቂቱ የሚከተሉትን ጽንሰ
ሃሳቦችና መርሆችን ብንመለከታቸው መስመር ሊያስይዙን ለመታገያና ለማታገያ መመሪያና መሳሪያ ሊሆኑን ይችላሉ። ከእነዚህም ጥቂቶቹ ለአብነት ያህል ራዕይ፣ ዕውቀት፣እምነት፣ተግባር፣አቅም፣ ጀግንነትና ጽናት ናቸው። እነዚህን መወያያ ነጥቦች የሚጠቀሱት በስፋት ለመተንተን ሳይሆን በአስተሳሰብና በስነምግባር ላይ ተጽዕኖ እንዳላቸው እንድንገነዘብና በትግላችን ላይ ሊነጸባረቁ ስለሚችሉ መመርመርና መፈተሽ ያስፈልገናል በሚል ነው። በአጠቃላይ ወደፊት በጥልቀት ሊታዩ የሚገባቸው ነጥቦች ቢሆኑም ለግዜው ግን ለምንፈልገው አስቸኳይ መፍትሄ ጠቋሚ የሃሳብ ንጥረት የሚፈጥርመቀስቀሻ መሳሪያ እንዲሆነን በሚል ነው የማቀርበው ። ራዕይ
ራዕይ ሳይኖር ሕዝብ መረን ይሆናል፣ ምሳሌ 29:18  በዓይነ ህሊናችን ቀርፀን ፣በአእምሮአችን አምነን፣ በተግባራችን ስንቀሳቀስ የተለምነውና የተመኘነውን
እናገኛለን።ራዕይ ማለት የማይታየውን ወይንም የወደፊቱን ሁኔታ አሁን ሲከሰት የማየት ልዩ ጥበብና ችሎታ ነው። ራዕይ ተጨባጭ ዕውነታ የሚሆነው ፣ ራዕይ ያላቸው ወይም ራዕያዊ ግለሰቦች ስመሩትና ሲመሩበት ብቻ ነው። በአጠቃላይ ራዕያዊ ግለሰቦች የሂደታቸውን መጨረሻ ግብ ከወዲሁ ከመነሻው መዳረሻውንና ፍጻሜውን የማየት ችሎታ አላቸው። ከትግላችንም አንጻር የእኛ ራዕይ የግባችን መዳረሻ የኢትዮጵያ ሕዝብ ድልን በእርግጠኝነት እንደምንቀዳጅ በዓይነ ህሊናችን ዓይተን: በሙሉ ልብ አምነን
: ለአሸናፊነት በተግባር ሲያሰማራን ማለት ነው። ይህ ታላቅ ጸጋ የተሰጣቸው ራዕያዊ ሰዎች ጠንካራ ባህርያት አንዱ በዓላማና መርሆ መሳካት ላይ ፍጹም እምነት አላቸው። እምነታቸው በዕውቀት ተደግፎ፣ በጀግንነትና የታነጹ መሳሪያዎች ስላሉት ለብዙዎች የማይታየውን የወደፊት ድል ዕውን እንዲሆን የማድረግ ችሎታ አላቸው። ለዚህም ነው ምንም ብዙ ግዜ ቢወስድ እና መሰናክል ቢገጥመውም ራዕይ ያለው ሕዝብ አይጠፋም የሚባለው። ራዕይ ያላቸው ግለሰቦችና መሪዎች ከፍተኛ የስብዕና ሉዓላዊነት
ባህሪ አላቸው፣ለምንም ዓይነት ተጽእኖ ተገዥ እና ተንበርካኪ አይሆኑንም በዚህም ምክንያት የሕዝብን ታአማኒነት ያገኛሉ ። ራዕይ የተስፋ መሪ ብርሃንና መንገድ ገላጭ በመሆኑ፣ ከጨለማዊ ባህሪና ከተሸናፊነት መንፈስ ጋራ አይሄድም ፣ተጻራሪ ነው።
ከተነሳንበት ዓላማ አንጻር ጥያቄው፣ ዛሬ ለይስሙላ ከሚነገሩ ባዶ ቃላት ባሻገር በእርግጠኝነት ለድል የሚያበቃን ራዕይ ያላቸው የፖለቲካ ድርጅቶች ሆኑ ራዕያዊ ባህርያትን የሚያሳ ዩግለሰቦችና መሪዎች አሉን ወይ ነው? ከሌሉስ እንዴት መፍጠር ይቻላል ነው?ዕውቀት-ራስን ማወቅ ዕውቀት፣ ሰፊና ጥልቅ የሆነ ርዕስ ነው። ሆኖም የዚህ ጽሁፍ ዓላማን ለመመለስ ያህል ራስን የማወቅ የሚለውን የዕውቀት ክፍል እናያለን ፣ ራስን ማወቅ የዕውቀት ሁሉ መሰረት፣ በግዜና በቦታ የሚወሰነውን
ስጋዊ አካላችን ከረቀቀውና ከማይታየው ውስጣዊ ስነልቦናዊ አካላችን ጋር የሚያገናኘን ድልድይና ማንነትን የሚያሳይ መነጽር ነው።ይህ ዕውቀት በግለሰብም ሆነ በጋራ ማንነት ላይ ሊኖረንና ልንጠቀምበት የሚገባ መሳሪያ ነው። ራስን የማወቅ ዕውቀት አካላዊና ቁሳዊ ፣ በዲፕሎማና በሞያ ምስክር ወረቀቶች የሚገመት ዕውቀት አይደለም። ራስን ማወቅ ዕውቀት የነጻነት መሰረት ነው። ለራሳችን ሆነ ለማህበራዊ ሕይወት አጠቃላይ የምንሰጠው ዋጋ የሚለካው ባለን የራስ ማወቅ የዕውቀት መጠን ነው። ዛሬ በርካታ
ኢትዮጵያውያን በዘመናዊ ትምህርት አማካኝነት የሞያ ዕውቀት ብንገበይም ራስን የማወቅ ዕውቀት ስለሚጎለን ወይም የተዛባና የተሳሳተ ዕውቀትን የሸመትን በመሆኑ የማህበራዊ ችግሮቻችን ማባባስ እንጂ መፍታትና ማስወገድ እንዳንችል አድርጎናል። ያከማቸነው ዕውቀት የተዛባና የተሳሳተ ብቻ ሳይሆን ፣ በሌሎች ባዕድ ማንነትና ምንነት ፣ጥቅምና ፍላጎት ላይ የተመሰረተ የሃሰት ዕውቀት ነው።
ራሳችንን በትክክልና በሃቀኝነት ብናውቅ ኖሮ ፣ዛሬ ካለንበት ሁኔታ ላይ አንደርስም ነበር፣የኢትዮጵያውያን ሕይወትና ዋጋና ክብርንም ጠንቅቀን እናውቅ ነበር። ለምሳሌ ባለፉት ሃያሁለት ዓመታት ውስጥ የተከሰቱት የፈረንጅ ፣የአረብ፣ የቻይና ወዘተ አምላኪነት እና የበላይነት የመቀበል አዝማሚያ አይንጸባረቅም ነበረ። ራስን የማወቅ ዕውቀት ከተዛነፈ ሌሎች ዕውቀቶችም ይበረዛሉ፣ መሰረታዊ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችል ሙሉ ኃይልና ጉልበት አይኖራቸውም። ስለዚህ ራስን የማወቅ ዕውቀት ወሳኝና ጠቃሚ ፣ለችግራችን መፍትሄ መሳሪያ ነውና፣ወደ ፍትህና ነጻነት በፍጥነት እንድንሸጋገር ፣ወደ ራሳችን ውስጣዊ የማንነት ዕውቀት በመመለስ ውስጣዊ ጉልበትን እናገኛለን። ራስን የማወቅ ዕውቀት የችሎታና የአቅም የጀግንነት መገኛ ኃይል ነው።ስለዚህም ወደ ወቅታዊው ጥያቄ በመመለስ ኢትዮጵያን ነጻ ለማውጥት የተነሱ የፖለቲካ ድርጅቶች መሪዎችና ግለሰቦች እስከምን ድረስ ነው ይሄን ራስን የማወቅ
ዕውቀት ያላቸው ወይም በተግባራቸው የሚያንጸባርቁት? በእርግጥ እነዚህን ጥያቄዎች አንስተን መፈተሽና መመለስ ይኖርብናል።
ራስን የማወቅ ዕውቀት አጥብቀን ብንይዝ ኖሮ በማንነታችን እንረካ ነበረ፣ የራስን የማወቅ ዕውቀት የተሳናቸው ሰዎች በቀላሉ የሌሎች ተከታይ በመሆን ለባርነትና ለመከራ ራሳን አሳልፈው ያጋልጣሉ። እንዲሁም ተጨቋኝም ሆነ ጨቋኝ ፣ ተበዳይም ሆነ በዳይ፣ ባጠቃላይ በአንድ ሥርዓተ ማህበር ውስጥ የሚገኝ ህዝብ የሚያንጸባርቀው ባህል፣ የስነ አእምሮ ባህርያትና ስነምግባር ለችግርም ሆነ ለመፍትሄ በአሉታዊም ሆነ በአዎንታዊ መንገድ ተጽኗዊ አስተዋጽዎ ያደርጋል። ለምሳሌ አንድ ማህበረሰብ ሆነ
ድርጅት ፍትህ ርትዕ አጉዋደለብኝ ወይም ጨቆነኝ የሚለውን በዳዩን ኃይል በተዛባ ምክንያት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ለጠላቱ ተባባሪና አጋዥ ይሆናል። ለዚህም ነው ጨቋኝ ገዥዎች በራሳቸው ኃይል ብቻ ሳይሆን በአብዛኛው ከተጨቋኙ ህዝብ መሃል በሚፈጠረው የስነልቦናና የስነ አእምሮ ድክመትን በመጠቀም ለረጅም ግዜ በግፍ ሊገዙ የሚችሉት። ይባስ ብለን ችግራችን ምክንያት የሆኑትን ኃይሎች ከችግራችን እንዲያድኑንና እንዲረዱን እንፈልጋለን። በብልሃትና በጥበብ መታገል ተገቢ ሆኖ ሳለ ፣
የምንታገለውን ኃይል እያስፈቀድንና ስሜቱን እየጠበቅን መታገል ግን በራስ ላይ መቀለድ ይሆናል።
እምነት ለተግባር የሚያዘጋጁ ሃሳቦች አንጻር ሲታይ፣ እምነት ማለት ስለሆነውና ስለምንሆነው ሆነ ስለምናከናውናቸው ነገሮች ሁሉ ከመሆኑ በፊት ሆኖ እንደተገኘ የምንቀበልበት የተስፋ መሳሪያ ነው።
ዓላማን ፍላጎትንና ምኞትን ወደ ተግባር የምንቀይረውና እውን እንዲሆን የምናደርገው ባለን የእምነት ጥራትና ጥንካሬ መጠን ላይ በመመስረት ነው ።ስው የሚያስበውን ይሆናል፣ የተመኘውን ያገኛል እንደሚባለው ሁሉ ፣ዛሬ በትግላችን ሂደት ላይ የምንመኘው ዓላማ ያልተሳካው አንደኛው ምክንያት ፣ለተግባራችን ምርኩዝ የሆነው እምነታችን እየተሸረሸረ በመምጣቱ ነው። በዓላማውና በዕቅዱ መሳካት ላይ እምነት የሌለው ትግልና ንቅናቄ ፍሬያማ ወይም ውጤታማ አይሆንም ፤ውስጣዊ ቅራኔን አዝሎስለሚጓዝ። የወያኔ የጎሳ አገዛዝን ምንነት በንግግራችን የምንገልጸው ትክክለኛ እምነታችንን አንጸባራቂ መሆኑን የምናውቀው በተግባራችን ዓላማችንን ሳያስለቅቅ ከአቋማችን ሳንዛነፍ ስንራመድ ነው።
በተነሳንበት ዓላማ ላይ ጠንካራ እምነት ከሌለን ወደ ወሳኝና ቁርጠኛ ተግባራት አንሸጋገርም። እምነት የተግባር መሪ አንቀሳቃሽ ኃይል ነው። ዛሬ ግን በትግላችን ውስጥ ይህ አይስተዋልም፤ ስለዚህ ጥያቄው ፀረ ወያኔ የኢትዮጵያ አንድነት ድርጅቶችና ግለሰቦች በሚያነሱዋቸው የፖለቲካ ጥያቄዎች ላይ ምን ያህል እምነት አላቸው ነው?ለምሳሌ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ህልውናና ሕዝባዊ አንድነትን የሚያምኑ ድርጅቶች
ይሄ ዋና የትግል ግባችን ነው ብለው የሚያምኑትን ዋንኛ ሃሳብ ግባቸውን ከሚጻረሩ ኃይሎች ጋር እንዴት ነው የኢትዮጵያን አንድነት ለማረጋገጥ ሕብረት የሚፈጥሩት? የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው የሚለው ድፍን ሃሳብ ለድል ያበቃናል ወይ?የምንመራበት የትግል ዓላማና የሃሳብ ጥራትና ትክክለኛነት ላይ ምን ያህል እምነት አለን?
ተግባር ለማንኛውም የህይወት ህልውና ተግባር ወይም ስራ ከሚያስፈልጉት የተፈጥሮ ህግጋት አንደኛውና ዋናው ነው። ራዕያችንም ሆነ ዓላማችንን የሚያሳኩት ልዩ ልዩ መሳሪያዎችን እውን የሚሆኑት በተግባር ሲተረጎሙና በስራ እቅድ በግዜና በቦታ በቅደም ተከተል ሲከናወኑ ነው። ከስራዎች ሁሉ የመጀመርያው ተግባራችን የሚሆነው ሃሳብና አስተሳሰብን ጥራትና ትክክለኛነትን እንዲይዝ ማድረግ ነው። አንድ ንቅናቄ
ወይም ዓላማ ስለሂደቱ መሰረታዊ ግንዛቤ ከያዘ በኋላ ወደ ቀጣዩ ተግባር መሸጋገር ይኖርበታል። አሁን ካለንበት ቦታ እና ሁኔታ ወደሌላና ወደምንፈልገው አቅጣጫ የማይወስደንን ተግባር ከቀጠልን ውጤታማ ስራ ሳይሆን ፣ ከንቱ መዳከርና መላሸቅን ያስከትላል ፣ ግዜንና ጉልበትን በከንቱ ያባክናል ፤ ብሎም የትግሉን አቅም መጉዳት ብቻ ሳይሆን የሕዝብን ተስፋ እንዲመነምን ያደርጋል። በየግዜው ስምና ቅርጽ እየቀያየረን ድርጅት ብናደራጅ ፣በህብረት ብንቀናጅ ፣ብንሰባሰብ ፣ ብንወያይ ወዘተ ለወቅታዊ የስሜት ፍጆታ ካልሆነ በስተቀር ላለንበት ችግር መፍትሄ ሰጭ ተግባር አልታየም፤በብዛት የምንሳተፍባቸው ተግባራዊ መሰል እንቅስቃሴዎች የምንቃወመው ኃይል በየግዜው የሚያደርስብንን የግፍና የጥፋት ተግባራት በመተንተንና በማውገዝ እንጂ በራዕያችን ላይ ያተኮረ በራሳችን መርሃ ግብር የሚመራ ተግባራዊ ክንዋኔ ላይ አይደለም። በተጨማሪም ስራ ተግባራዊ የሚሆነው ስራውን በሚሰሩት ግለሰቦች
ወይም ማህበረሰቦች የባህርያት ጥንካሬና ሉዓላዊነት ላይ ሲመሰረት ነው። ለምሳሌ ለዘብተኛ ወይም ጽናት የሌለው ወላዋይ ባህሪያት ያላቸው ግለሰቦች ሆነ ድርጅቶች ዘላቂ ተግባራዊ ለውጥን ማምጣት አይችሉም፣ ወይ አይሞቁ ወይ አይቀዘቅዙ እንደሚባለው፣ የለዘበ ተግባር ማለት እምርታን የማይሰጥ ከአንድ ደረጃ ወደ ሌላ የማያሸጋግር አዘናጊ ስራ ነው። ጥያቄው በውጭም ሆነ በሀገር ውስጥ ያሉና የተደራጁ ተቃዋሚ ኃይሎች እምነታቸውና ተግባራቸው ምን ያህል ይንጸባረቃልና ይመጣጠናል ነው? የወያኔ የጎሳ አገዛዝ ለአገራችንና ለሕዝባችን መጥፎ ስርዓት ነው ሊወገድ ይገባል ብለን ካመንን የሚያስፈልገውን አጸፋዊ እርምጃ መውሰድ ተገቢ የትግል ስልት
መሆን ይኖርበት ነበር። በአንጻሩ የምንመለከተው ግን ተቃዋሚ ድርጅቶችና ኃይሎች እንኩዋን አጠፌታውን ተግባር መመለስ ቀርቶ በወያኔ ላይ ጨክነው የኢኮኖሚና የፖለቲካ ማዕቀብ ማድረግ እንኩዋን አልቻሉም።
ጀግንነት
ጀግንነት ብዙ ግዜ በጦርነት ሜዳ ላይ ወይም በግጭት ወቅት ብቻ የሚገለጽና የምንጠቀምበት ባህሪ ይመስለናል፣ ነገር ግን ጀግንነት በሁሉም የኑሮ መስክ ውስጥ በግልም ሆነ በጋራ በቀን ተቀን ህይወታችን ውስጥ የሚገለጥ ልዩ መለያው ቆራጥነት አልበገሬነትና ፍርሃትን አቸናፊ ባህሪ ነው።ጀግንነት በምናስባቸው ሆነ በምናደርጋቸው ተግባራት ሁሉ ያለፍርሃት የሚያተኩረው ሊፈጠሩ በሚችሉ የውድቀት ሃሳቦች ላይሳይሆን በአቸናፊነት በሙሉ ልብ አምኖ ፈር ቀዳጅና ፋና ወጊተግባራትንእንድንፈጽምየሚያስችለን ልዩ የስሜት ባህርይ ነው። ለዚህም ነው ጀግና የማይወደውንና የማይፈልገውን፣ ስብዕናውን በማንኛውም መንገድ ለሚደፍር አመለካከትና ተግባር አይበገርም፣ አያጎበድድም የሚባለው። ጀግንነት ነገሮችን ለመቀየር ከምንጠቀምባቸው መሳሪያ መሆኑ ብቻ ሳይሆን መከላከያም ጭምር ነው።
ኢትዮጵያውያን ዛሬ ይህንን መሳሪያ ማጣታችን ገሃድ ነው።
ኢትዮጵያውያን በጀግንነትና በልበሙሉነት በሀገር ውስጥ የተንሰራፋውን የግፍ አገዛዝ ከማስወገድና ከመቋቋም ይልቅ መሸሽና መሰደድን መርጠናል።የተሰደደውም ህዝብ በውጭ አገር ስለተገኘ ጀግና ይሆናል ማለት አይደለም ያንኑ የፍርሃት ፀባይ ይዞ ነውና የተሰደደው ።በውጭ ሀገር በየፖለቲካ ድርጅቶችና ንቅናቄዎች በሰፊው ተንጸባርቆ የምናየው ዕውነታ ይህ ነው።አሁንም በፍርሃት ቆፈን የታሰረ ስለሆነ ፣ በቆራጥነት በያለበት ቦታ እንዳይታገል የተለያዩ ምክንያቶች በመደርደር ውጭ ያለው ትግሉ
አገርቤት ነው ሲል፣አገር ቤት ያለው ተቃዋሚ ነኝ የሚል ኃይል ደግሞ እንዳይታገል ወያኔ ያስራል ፣ አይፈቅድም፣ነጻነት የለም ወዘተ በሚል ምክንያት ትግሉን በማጓተት የግፍ አገዛዙን ዕድሜ ያራዝማል።
በሀገር ውስጥ ሆነ በውጭ ሀገር ጀግንነት በውስጣቸው የሌላቸው ግለሰቦች ፣ቢሰባሰቡና ቢመሩም ጀግኖች አይሆኑም፣ በብዙ ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ የምናየው ሃቅ ይኸው ነው። ጥያቄው በአገራችን ወቅታዊና ተጨባጭ ሁኔታ አኳያ ሲታይ ዛሬ የገጠሙንን የውጭም ሆነ የውስጥ ጠላቶች ለመቋቋም የሚያስችል የጀግንነት ስራና ባህርይ አለን ወይ? ነው።በተለይም በአሁኑ ግዜ የወያኔን የጎሳ አገዛዝን ለማስወገድ በሚደረገው ፍልሚያ በሁሉም የትግል መስክ በቆራጥነት የሚታገሉ ድርጅትች ፣ንቅናቄዎችም ሆኑ
ግለሰቦች አሉን ወይ ብለን በመጠየቅ መለስ ልንሰጥ ይገባል።
አቅም ከላይ ከተጠቀሱት አስፈላጊ ጽንሰ ሃሳቦች በተጨማሪ አቅም ለውጥ ለማምጣትና ለተግባራዊ ብቃት ከሚያስፈልጉ ነገሮች ውስጥ ዋና መሳሪያ ነው። የአቅም ምንጭ የሆነውን እውቀትና ጥበብን በሚጠቅም መንገድ መጠቀም መቻል እራሱ አቅምን መገንባት ነው።ከሁሉም የበለጠ ለማንኛውም ተግባር ወሳኙ አቅም የሰው ኃይል ነው። ይህም አቅም የሚገኘው በአጠቃላይ ከብዙሃኑ ህዝብ ሲሆን በተለይ ደግሞ ከተወሰነ ማህበረሰብ፣ ለምሳሌ ከምሑር ፣ከወጣቱና ከ ሴቶች ነው። ለትግል የሚያበቁ የመታገያ መሪ ሃሳቦችንና የስነምግባር መርሆችን መቅረጽ ፣ የተማረው የህብረተሰብ ክፍል ከፍተኛ ሃላፊነት ነው።የወያኔ የጎሳ ፍልስፍናን መሰረት ያደረገ ፖለቲካ በተሳሳተና በሃሰት ላይ የተዋቀረ ታሪክ መሆኑን በድፍረትና በሃቀኝነት ማሳየትና ለድል የሚያበቁ የመታገያ ጽንሰ ሃሳቦችም ሆኑ ጥያቄዎች ህዝባዊ እንዲሆኑ ማድረግም የተማሩ ሰዎች ተግባር ሊሆን ይገባል። ሌላው የአቅም ምንጭ ወጣቶች በተፈጥሮ ባህርያቸው
የወደፊት ተስፋ በመሆናቸው የታመቀ የለውጥ ኃይልና የአቅም ምንጭ ናቸው። እንዲሁም የህብረተሰቡ ብዙሃን ክፍል የሆኑት ሴቶች የህብረተሰብና የቤተሰብ ዋልታና ምሶሶ በመሆናቸው ለትግሉ ወሳኝ አስተዋጽዖ ማድረግ የሚችል የአቅም ኃይል ናቸው።እነዚህ ዋና የሕዝብ ክፍል ለወያኔ ጎሰኛ አገዛዝ ሰለባ በመሆን በአገር ውስጥም ሆነ በስደት ለችግር እንዲጋለጡ ሆነዋል ። ወያኔን የሚቃወሙ ኢትዮጵያዊ
ድርጅቶችስ ምንያህል ይሄን ወሳኝ አቅም በተለይም ሴቶችን በትግሉ ሂደት ውስጥ ያሳትፋሉ?ሌላው አቅም አባካኝ ተግባር እንዳውም ለትግሉ የሚጠቅሙትን ግለሰቦች ሆነ ድርጅቶች እንደማሰባሰብ ፋንታ ወያኔያዊ አስተሳሰብ ያላቸውን፣ ከወያኔ ጋር አብረው ህዝብን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የበደሉ ፣ጽናት የሌላቸው ፣አድርባዬችን፣ክብርና ዋጋ በመስጠት የተበላሸ የባህል አሴቶች እናስፋፋለን።የአቅምን ምንጭ በትክክል አለማወቅና አለመጠቀም ዛሬ ለደረስንበት ውድቀት እንዳደረሰን ሁሉ ፣ከችግራችን መውጪያ መፍትሄም መሆኑን ልንገነዘብና ተግባራዊ ማድረግም የግድ ይላል።
ጽናት
ማንኛውም ዓላማ ግቡን ለመምታት በመጀመር ብቻ ሳይወስን እስከ ፍጻሜ የመቆየትን ችሎታ ይጠይቃል።ይሄም ልዩ ችሎታ ጽናት ነው። በጽናት ያልቆመና የማይጓዝ ትግል ጉልበትና ግዜ በከንቱ አባካኝና የራስን ዓላማ አሰናካይ በሆኑ ምግባሮች ላይ እንዲያተኩር ይሆናል። ከጽናት መላላት የተነሳ ብዙ የተዛቡ ትርጉም የለሽ ስራዎች ይሰራሉ ። ላምሳሌ ወያኔን በመቃወም የሚታገሉ ድርጅቶች ወያኔየሚያምንበትን ፍልስፍና ከሚከተሉ ጋር መተባበር ለወያኔ እንጂ ለተቃዋሚ ኃይል ጥቅም የለውም ፣
ሆኖም ግን ዛሬ ተቃዋሚ ነን የሚሉ ኃይሎች በዚህ ተግባር ተጠምደው እናያለን። በሬ ካራጁ ይውላል እንደሚባለው ሁሉ ለአንድነት የሚታገሉ ኃይሎች አንድነትን ከሚቃወሙ ጋር መተባበር ፣ ማለትም የሃሳብና የመርህ አንድነት የሌላቸው የራስን አቋም ከሚጻረሩ ድርጅቶች ጋር ለማስተባበር የሚደረገው ፍሬቢስ ተግባር ለሃያ ሁለት ዓመት ተሞክሮ ያልሰራ ሂደት ነው።በጸረ ወያኔ ትግል ውስጥ የሚደረገው ጠላትና ወዳጅን በቅጡ ካለመለየት የተነሳ፣አጋር ኃይልንም እንደ ጠላት እናጠቃለን። ጨለምተኛ በሆኑ አመለካከቶች፣ራሳችንን ስንነክስ ስናቆሽሽና ስናዋርድ እንገኛለን፤ ለትግላችንም አሉታዊ ውጤትን የሚያስከትል የስንፍናና የደካሞች ባህሪ ነው።በአንጻሩ ግን ጠላት ለሚባልለውና ግፍ ለሚያደርሱብን ሲበድሉ ለነበሩት የማያስፈልግ ትግስትና መቻቻልን እናሳያለን።ብዙ ግዜ ይህ ዓይነት ጸባይ ከጽናት መላላትና መቦርቦር የተነሳ የአዕምሮ ተገዥዎች የሚያሳዩት የተሸናፊ ባህርይ ነው። ለምሳሌ
የኢትዮጵያውያን የሚለው ራሳችንን ገላጭ የመጠሪያና የማንነት ስማችን ቀስ በቀስ ሃበሻ በሚል ስም እንዲተካ መደረጉ በጽናት ጉድለት የሚመጣ ደካማነት ነው። ሌላው ለአብነት የሚጠቀሰው ኢትዮጵያዊነትን ከማዳከም ጋር የተያዘው አደገኛ ሂደት በፖለቲካም ሆነ ፣ በድህነት ምክንያት ተሰዶ በውጪ አገር የሚገኘው ኢትዮጵያዊ የመጣበት ቦታና መመለሻ አገር እንደሌለው የተበተነ ሕዝብ መጠሪያ ራሱን ዲያስፖራ እያለ ይጠራል። ይሄም ሆነ ሌሎች ለራሳችን የማይጠቅሙ ተግባራት የሚንጸባረቀው በጽናት ስላልተገኘን ነው።ስለዚህ በልበ ሙሉነት አገራዊና ማህበራዊ ትግላችን እንዲሳካ
በጽናት በዋናነት በራሳችን ዕምነት ስንመራ ነው።
መደምደሚያ: ስራ የጀግና ድል የእግዚአብሄር ነው።
ከላይ እንደተጠቀሰው የዚህ ጽሑፍ ዋና ትኩረት አሁን ለምንገኝበት ወቅታዊና አጣዳፊ ውስብስብ ቀውስ መፍትሄ ለማግኘት ቁልፍ የሆኑትን የችግሮቻችን ባህርያት እና መገለጫዎችን እንድንገነዘብና አስፈላጊውንም ቀጣይ እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችሉንን ሁኔታዎች ለመፍጠርና ለማመቻቸት የሚያስችል ጥያቄዎችን ለማንሳት ነው። ትኩረታችን በሃሳብም ሆነ በተግባር አቅጣጫ የሚቀይስ ለግብ በየሚያበቁን መርሃ ግብሮች ዙሪያ ጥያቄዎችን በአዎንታዊና በቀና መንገድ በማንሳት ለመመለስ
እንዲያስችለን ነው። የትግላችን መንስኤ ምክንያቶችና ግባችን ምንድናቸው ፣ለምንስ አልፈታናቸውም ፣ አሁንስ እንዴት እንፈታቸዋለን?ወያኔን መጥላትና መቃወም ብቻውን መፍትሄ ሊሆን ይችላል ወይ ?ኢትዮጵያና ሕዝቧን በትግሉ ቀዳሚና ማዕከላዊ ቦታማስያዝ የምናስችለው እንዴትነው የሚሉት
ጥያቄዎችን መፈተሽ አስፈላጊ የትግሉ አካል ነው።
ለመልሳችን መንደርደሪያ የምንፈልገውን ለውጥ ሊመጣና ችግሮችን ልንፈታ የምንችለው፣ በተጎጂ ሰነልቦናዊ ስሜት ተመርኩዘን ሳይሆን በራሳችን ውስጣዊ አዎንታዊ የአስተሳሰብ ጥራትና ጥንካሬ ላይ ተግባራችንን ስንመስረት ነው።ይህም ማለት የመፍትሄ ምንጭ መሆን የምንችለው ፣ በራሳችን ስለራሳችን ህልውና ወሳኝ ኃይል መሆናችንን ስንገነዘብና ሙሉ በሙሉ ስናምንም ጭምር ነው።
አዲስ እና ለየት ያለ ድፍረትንና ቆራጥነትን ከሚጠይቅ ፣ለለውጥና ለመፍትሄ ከሚያበቁን ተግባራዊ መንገዶች ከመቀጠል ይልቅ፣ በብዛት ተቃዋሚ የሚባለው ኃይል የሚያደርገው ትግል ፣የሚመቸውንና የለመደውን መስዋዕትነት የማይጠይቀውን ስራ በማካሄድ ላይ ያተኮረ ነው። እምነት ያለ ተግባር ፣ተግባር ያለ እምነት ከንቱ ነው እንደሚባለው ፤ የዓላማና የአስተሳሰብ ጥራት ፣ የርዕዮትዓለም ትክክለኛነት
ያለተግባር ከንቱ ነው። እንዲሁም ተግባር ያለ ጠንካር እምነትና መሪ ሃሳብና ራዕይ ትርጉም የለሽ ፍሬቢስ ስራ ይሆናል። ተግባራችን ከሚመራበት ውስጣዊ እምነታችን ጋር ሳይጋጭ ፣ሚዛናዊና ጊዜያዊ ሁኔታዎችን በማጣጣም አዋህደን ስንሰራ ፣የተነሳንበት ዓላማና ራዕያችን ይሳካል።ከላይ የተጠቀሱትን ጽንሰ ሃሳቦች በመሳሪያነት ከያዝንና ቆርጠን ከተነሳን የኢትዮጵያ ሕዛብ ድል በኢትዮጵያውያን እጅ መሆኑን እናረጋግጣለን። በአንድ ልብ ከተሰራ ሁሉ ነገር ይቻላል የሚለውን መርህ ዕውን ልናደርግ እንችላለን።
ስራ የጀግና ድል የእግዚአብሄር ነው።
ዶ/ር አበባ ፈቃደ

No comments:

Post a Comment