Wednesday, August 21, 2013

የኢሳት የውይይት መድረክ ከየት ወዴት!!?

ይህ ርዕስ እጅግ ሰፊ በመሆኑ በቀጣይነት ብዙ ልንወያይባቸው የሚገቡ ሃሳቦችን ይጠቁማል፤ እኛም ለወደፊት በዚህ ጉዳይ ዙሪያ ብዙ የምንል መሆኑን ከወዲሁ ማሳወቃችን አስፈላጊ ነው። ስለሆነም ለመንደርደሪያነት ይጠቅም ዘንድ ለዛሬ ሃሳባችንን ባጭሩ እንደሚከተለው ጠቆም አርገን ማለፍ ግድ በመሆኑ አነሆ እንላለን።
የኢሳት ሬድዮና ቴሌቪዥን ትላንት እሁድ በአሜሪካን ሃገር በዋሽንግተን ዲሲ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ የሚያወያይ ስብሰባ ማዘጋጀቱን ሁላችንም ሰምተናል፣ አይተናልም። ይህ ዝግጅት ሁሉንም የኢትዮጵያውያን አስተሳሰቦች ለማስተናገድና፤ ልዩነቶችን በውይይት በመፍታት በጋራና በቅንጅት ትግሉን በማስኬድ፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ካለበት የኢህአዲግ የባርነት አገዛዝ ቀንበር ውስጥ ለማውጣት፤ ብሎም የሃገራችንን እንደ ሃገር የመቀጠል ህልውና ከጥፋት ለመታደግ በሚል ቅዱስ ሃሳብ የተነሳ በመሆኑ፤ እሰየሁ ሊባል እንደሚገባ ሁላችንንም ያስማማል። በተለይ ባሁኑ ጊዜ ለኢትዮጵያ ህዝብ ሰቆቃ ዋናው ምክንያት፤ ለሃገሪቱም መጥፋት ሌት-ተቀን የሚሰራውን ኢህአዲግን መጋበዙ ትልቅ ቦታ ሊሰጠው ይገባል።

ሁላችንም እንደምናውቀው ሁሉም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ተቃዋሚ ሃይሎች በተደጋጋሚ እንደሚነግሩን፤ “ገዢው ፓርቲ ለውይይት ፈቃደኛ አይደለም፤ ተወያይተን መፍትሄዎችን በጋራ እናምጣ ብለን በተደጋጋሚ ብንጠይቅም ኢህአዲግ ፊቱን አዙሮብናል፤…” ሌላም ሌላም ተመሳሳይ ወቀሳዎችን ሲገልጹ ማየትና መስማት ለኢትዮጵያውያን አዲስ አይደለም። በሌላ በኩል ደግሞ ኢህአዲግ የሃገሪቱን ሰላምና ደህንነት በአስተማማኝ ለመጠበቅ በሚል ሰበብ የጎረቤት ሃገራትን ፤ ኤርትራን ጨምሮ ፤ ዳጎስ ያሉ ጉርሻዎችን እያቀረበ ሲማጸን ማየቱ ለኢትዮጵያውያን የተለመደ ትዝብት ሆኗል። እንደኛ አረዳድ ይህን መሰሎቹ የተቃዋሚ ሃይሎች ወቀሳዎች እውነት ከሆኑ፤ የኢህአዲግ መንግስት ያልተረዳው ዋናው ቁምነገር፤ ማንኛውም የሃሳብ ልዩነት በመወያየት ወደ ስምምነት መምጣት ካልተቻለ፤ ወደ ሌላ ትልቅ ልዩነት አድጎ ሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚመኘውን ዘለቄታዊ ሰላም ማምጣት ፈጽሞ አስቸጋሪ ሊሆን እንደሚችል ነው። በርግጥ ኢህአዲግ የተሳነው የፖለቲካ ተቃዋሚ ሃይሎች የሃሳብ ጉልበትን መለካትና ማወቅ መቻል ነው። ነገር ግን አበው “የናቁት…” እንዲሉ ከኢህአዲግ ልንማርና አካላዊ የጉልበት ልዩነቶችን ከማስተናገድ ይልቅ የሃሳብ ልዩነቶችን ለማስተናገድ ብንጥር የተሻለ ነው እንላለን።
ይህንን የኢሳት መድረክ የዝግጅት ሂደቶችን በተመለከተ ብዙ የታዩ የግድፈት መረጃዎች ቢኖሩንም ብዙ ከማለት መቆጠቡ ለጊዜው አስፈላጊ ስለመሰለን ወደ ዝርዝር ሁኔታዎች አንሄድም። ነገር ግን እዚህ ላይ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ፤ የኢህአዲግ ካድሬዎች እንደሚሉን “ሺሺ… ፈሳም አንድ ጎማ አይነፋም…” ሊሆን ስለሚችል፤ ኢሳቶችም ይህንን ማሰብ ይችሉ ዘንድ እንመክራለን። የኢህአዲግ መንግስት በህዝብ ላይ እየጫነ የሚገኘውን ስቃይ፣ መከራ፣ እንግልት፣ ግድያ ፣ እንዲሁም ሌሎች አሰቃቂ በደሎችን ለማስቆም በጋራ መፍትሄዎችን እንፈልግ ዘንድ እናሳስባለን።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!
ስምንቶቹ

No comments:

Post a Comment