Wednesday, August 7, 2013

የመላው ኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ኦህዴድ የኦሮሞን ህዝብ ችግር አይፈታም አለ

መስከረም አያሌው

የኦሮሚያ ክልልን የሚያስተዳድረው የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) የተፈጠሩ ችግሮችን ለመፍታት በኃይል ላይ የተመረኮዘ መንገድ መጠቀሙ የኦሮሞን ህዝብ ችግር መፍታት እንደማይችል ያሳያል ሲል የመላው ኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ገለፀ።
ፓርቲው ባወጣው መግለጫ ኦህዴድ የኦሮሞን ሕዝበ - ሙስሊም ጥያቄም ሆነ የአጠቃላይ የኦሮሞን ህዝብ መብት ማስከበር እና ፍላጎቱን የማሟላት የማይችል፤ እንዲሁም የህዝቡን ችግር መፍታት የማይችል ድርጅት ነው ብሏል። ድርጅቱ ጊዜ ካለፈበት በኃይል ችግርን መፍታት አሰራር ታርሞ ዘመናዊ ወደሆነው ዴሞክራሲያዊ መንገድ እንዲመጣም ፓርቲው ጥሪ አቅርቧል።
ድርጅቱ በአርሲ ዞን አሳሳ ከተማ የኦሮሞ ሙስሊምን ጥያቄ በጠመንጃ ለመፍታት ባደረገው ሙከራ የሶስት ሰዎች ህይወት መጥፋቱን፣ በበርካቶች ላይ የመቁሰል አደጋ መድረሱን እና ንብረትም መውደሙን የገለፀው ፓርቲው፤ ድርጅቱ ካለፈው ስህተቱ ሳይማር በአሁኑ ወቅትም ተመሳሳይ ድርጊቶችን እየፈፀመ መሆኑን ገልጿል። በዚህም ሳቢያ ችግሩ ተስፋፍቶ በሐምሌ 27 ቀን 2005 ዓ.ም በአሳሳ ከተማ፣ ከዚያ በፊትም በዶዶላ፣ በኮፈሌ እና በሻሸመኔ የህዝብ ሙስሊሙ ጥያቄ ሊቀሰቀስ ችሏል ብሏል።
“ኦህዴድ ከዚህ በፊት የፈፀመው ስህተት ሳያንሰው በአሁኑ ሰዓትም ለችግሩ መፍትሔ የጠመንጃ አፈሙዝ በመጠቀም በአስር ሰዎች ላይ ሞት እና በብዙ ሰዎች ላይም የመቁሰል አደጋ ደርሶባቸዋል” ያለው ፓርቲው፤ ኦህዴድ እየተጠቀመ ያለው የችግር አፈታት ዘዴ በኃይል ላይ የተመረኮዘ በመሆኑ ዛሬ ያለውንም ሆነ የወደፊቱን የኦሮሞ ህዝብ ችግር መፍታት የማይችል ድርጅት ነው ብሎታል። እየፈፀመ ያለው ድርጊት ከፍተኛ ስህተት ከመሆኑም ውጪ መፍትሄ የማያመጣ ስለሆነ ድርጅቱ ከድርጊቱ እንዲቆጠብ እና ለችግሩ በውይይት መፍትሔ እንዲፈልግ ፓርቲው ጨምሮ አሳስቧል።

ሰንደቅ ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment