Wednesday, September 25, 2013

ደመወዝ ስላልተከፈላት በሺዎች የሚቆጠር ገንዘብ የሰረቀችው ኢትዮጵያዊት ፍ/ቤት ቀረበች

በመስከረም አያሌው

ኢትዮጵያዊቷ የቤት ሰራተኛ በዱባይ ለሦስት ወራት ያህል የሰራሁበትን ደመወዜን አልከፈለችኝም ካለቻት አሰሪዋ በሺዎች የሚቆጠር ዶላር እና ድርሃም እንዲሁም ወርቅ በመስረቋ በቁጥጥር ስር ውላ ጉዳዩዋ እየተጣራ ይገኛል።
አሊ ሻውክ ሰቨን ደይስ የተባለው ድረ-ገፅ እንዳስነበበው የ22 ዓመቷ ኢትዮጵያዊት ከ41 ዓመቷ አሰሪዋ ገንዘቡን የሰረቀችው የሰራችበት ደመወዝ ስላልተከፈላት ያንን ለማካካስ መሆኑን ለፍርድ ቤት ገልፃለች። “አሰሪዬ ለሦስት ወራት የሰራሁበትን ገንዘብ አልሰጠችንም። ገንዘቡን የወሰድኩትም ስለፈለኩት ነው። ደግሞም ገንዘቡ የራሴ ነው” ስትልም ተናግራለች። የዱባይ ዐቃቤ ሕግ እንደገለፀውም ኢትዮጵያዊቷ 25ሺ ዶላር፣ 2ሺ 200 ድርሃም፣ 200 ዩሮ በካሽ የወሰደች ሲሆን፤ በተጨማሪም 8ሺ ድርሃም የሚያወጣ የወርቅ ጌጥ ወስዳለች።
የኢትዮጵያዊቷ አሰሪ ገንዘቡን እና ወርቁን ካስቀመጠችበት እንዳጣችው ወደ ፖሊስ እንደደወለች ተናግራለች። “ወደ መኝታ ቤቷ ስገባ የሆነ አዲስ ነገር ተገነዘብኩ። ሰው የተኛ ለማስመሰል ሞክራ ያስቀመጠችውን ትራስ ሁሉ ፈትሻለሁ። ነገር ግን ላገኛቸው አልቻልኩም” ብላለች። ከኢትዮጵያዊቷ በተጨማሪም ዜግነቷ ያልተጠቀሰ ሌላዋ ሰራተኛዋን ከቤት እንዳጣቻት የተናገረችው አሰሪ ሁለቱም ፓስፖርታቸውን ይዘው ከቤት እንዳመለጡ ለፖሊስ ደውላ ተናግራለች። ፖሊስም ሁለቱንም የቤት ሰራተኞች ተከታትሎ በመያዝ በቁጥጥር ስር ያዋላቸው ሲሆን፤ ጉዳያቸው በሀገሪቱ የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት እየታየ ይገኛል።

No comments:

Post a Comment