Sunday, September 29, 2013

ሐረግነት፣ አውራነት እና ውራነት!? (ከኤልያስ ገብሩ ጎዳና)

“ትግል እና ዕውቀት ከያ ትውልድ ጋር አላከተመም” እስክንድር ነጋ
እንደ መነሻ፡-
ኢትዮ-ምኅዳር ጋዜጣ በነሐሴ 15 ቀን 2005 ዓ.ም ዕትሟ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ነሐሴ 12 ቀን 2005 ዓ.ም በሠማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት ተጋብዘው “ኢህአዴግ በፖለቲካ ፍልስፍና አይን ሲዳሳስ” በሚል ርዕስ ያቀረቡትን ህዝባዊ ውይይት ለአንባቢያን በሚያመች መልኩ አስተናግዳ ነበር፡፡
እንደተገነዘብኩት፣ ዶ/ር ዳኛቸው መግለጽ የፈለጉትን ፍሬ-ሃሳብ በቀላሉ፣ በምሳሌ አዋዝተው፣ በአመክንዮ እና በተነፃፃሪነት የምሑራንን እና የፈላስፎችን ዕይታ ከነባራዊ የኢትዮጵያ ፓለተካ ጋር ቃኝቶ ለሁሉም በሚገባ መልኩ ማቅረብ አንዱ ተሰጥዎአቸው ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡
ዶ/ሩ በዚህ የመወያያ ርዕስ፣ ካነሷቸው አንኳር ጉዳዮች መካከል አንዲቷ ሃሳብ ይበልጥ ቀልቤን ገዛችው፤ ደጋግሜም አሰላሰልኳት፡፡ በማስለሰልም ብቻ አልተገታችም- ሃሳቧ፡፡ ከቅርብ ጓደኛዬ ጋር ስንወያይባት ነበር፡፡

ያኔ ቀልቤን የሳበችኝን የዶ/ር ዳኛቸውን ሃሳብ በወቅቱ አንስቼም ከገደኛዬ ጋር በንቃት ተነጋግረንበታል፤ በነጋታው ጥዋት ግን፣ የመሰጠችኝን ሃሳብ ወደ ጽሑፍ እለውጥ ዘንድ ውስጤ ባመለከተኝ መሠረት፣ ይኸው ዛሬ ሃሳቤን አሰፈርኩ፡፡
ዶ/ር ዳኛቸው በህዝባዊ ንግግራቸው የተቃውሞ ፓለቲካ ችግር፣ የፓለቲካ ቅቡልነት ማጣት መሆኑን ጠቅሰው፣ “አንዳንዶቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ የሐረግ ህልውና ነው ያላቸው፡፡ ሐረግ ለብቻው መቆም አይችልም፡፡ ግንብ ላይ ወይም ዛፍ ላይ መንጠልጠል አለበት፡፡ ሁልጊዜ ‹ሪአክቲቭ› ናቸው፡፡ ‹ኢህአዴግ እንዲህ አደረገ … እንዲህ አለ …› በማለት ሁል ጊዜ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ፣ የራሳቸውን ፕሮግራም፣ ማንፌስቶ እና ራዕይ ይዘው መሄድ አላባቸው፡፡ ይህ በጣም ወሳኝ ነው፣ ከሐረግ ህልውና መወጣት” ሲሉ አብራርተዋል፡፡
ግንቦት 14 ቀን 2005 ዓ.ም ለንባብ በበቃው ኢትዮ-ምኅዳር ጋዜጣ ላይ ዶ/ር ዳኛቸው “ተቃዋሚዎችና እና ገዥዎቻችንን ስናስተውል” በሚል ርዕስ ከላይ ከተጠቀሰው ጋር ተመሳሳይ የሆነ ሀሳብም አቅርበው ነበር – ተቃዋሚዎችን በቤት ውስጥ አትክልትነት በመመሰል፡፡
ዶ/ር ዳኛቸው፣ የተቃዋሚውን ኃይል ሲመለከቱ ለብዙ ጊዜ ዘለቄታዊና ጽናት ያለው ሊያስብል የሚችል የፓለቲካ ሀሳብ አመንጭተው ሲታገሉና ስርዓቱን በሚገባ የተረዳ ትንታኔ ሲያቀርቡ እንዳልተመለከቱ አስተውሎታቸውን ገልጸዋል፡፡ “ልክ የቤት ውስጥ አትክልት አፈርና ውሃ ከውጭ እንደሚመጣለት ሁሉ እነርሱም (ተቃዋሚዎች) ኢህአዴግ በተሳሳተ ቁጥር አፈርና ውሃ ይጨምርላቸዋል፡፡ ጊዜያዊ የሆነ ርዕስ ጉዳይ ይያዝና ትንሽ ‘ሆያ ሆዬ’ ይባልና ወዲያው ደግሞ ይከስማል፣ ይጠወልጋል”ተቃዋሚዎች ተጨባጭ አዎንታዊ ለውጥ ለማምጣት ከፈለጉ “ከቤት አትክልትነት” ወደ ተፈጥሯዊ (የእርሻ) ሜዳ መውጣት እንዳለባቸው የሚያስገንዝቡት ዶ/ር ዳኛቸው፣ ተቃዋሚዎች አፈርና ውሃ የራሳቸው በማድረግ እና ፀሐይዋንም ተሻምተው መጋራት መቻል እንደሚኖርባቸው አጽንኦት ሰጥተው ነበር፡፡ ይሄንን ሀሳብ እኔም እጋራዋለሁ፡፡ ሆኖም ከዚህ በተለየ ደግሞ የራሴን ዕይታ መጨመር ወደድኩ፡፡
ኢህአዴግና ሀረግነቱ
ሳስበው ሳስበው፣ እንደ “ሀረግ” ወይም እንደ “ቤት አትክልት” ሆነው የተገኙት አንዳንድ ተቃዋሚዎች ብቻ አይመስሉኝም፡፡ ይህችን አገር በዋነኘነት እንዳሻው ቤተ-ሙከራ በማድረግ እየዘወራት የሚገኘው ገዥው ፓርቲም ቢሆን “ሀረግ” እና የ “ቤት አትክልት” ከመሆን አላመለጠም ብዬ አስባለሁ፡፡
ከትግል ሜዳው ጀምሮ ወደ ተለያዩ ርዕዮተ ዓለማት እንደ ጅምናስቲክ እየተገለባበጠ በራሱ መቆም ያልቻለ ሀረግ እና በበረሃ የተፈጥሮ (የሜዳ) አትክልት መሆን ሳይችል አንዱን ሲይዝ እና አንዱን ሲለቅ ስልጣን መጨበጡን ማስታወስ ያሻል፡፡ ህወሓት /ኢህአዴግ ከአልባኒያ አብዮት፣ ወደ ነፃ ገበያ ካፒታሊዝም ሥርዓት መገለባበጡን ልብ ይሏል፡፡
በሌላም በኩል፣ ኢህአዴግ የቀድሞ ጠ/ሚ/ር መለስ ዜናዊ ከመሞታቸው በፊት እንደ ሀረግ ተጠምጥሞባቸው ሀገርን ሲመራ ቆይቷል፡፡ ከህልፈታቸው በኋላም በሙት መንፈሳቸው ላይ ጥገኝ ሆኖ ዛሬም እየኖረ ነው፡፡ ሐረግ! ደግሞ በሌላ በኩል፣ የኢህአዴግ መንግስት ጥገኛ ሆነው በ “ሀረግነት” እና በ “ቤት አትክልትነት” እድሜ እያስቆጠሩ የሚገኙ ኤፈርትን የመሳሰሉ ኢንዶውመንት ድርጅቶችን የኢትዮጵያ እጆች አቅፋ ትገኛለች፡፡ እነዚህን መሰል ተቋማት እና ድርጅቶች “ታላቁ” ፓርቲ ስልጣኑን በሚያጣበት ጊዜ መጠውለጋቸው፣ መድረቃቸውና መክሰማቸው አይቀሬ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም በሕዝባዊና ሀገራዊ መሠረት ላይ አላቆማቸውምና፡፡
ሐረግነት በዚህም ብቻ አይቆምም፤ ዘርፈ ብዙ ነው፡-
በመንግስት እና መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች ውስጥም፣ ባለ ወይም ባሉ ጥቂት ጠንካራ ሰዎች ላይ ብዙሃን ሰራተኞች ጥገኛ ሆነው የመታየታቸውም ሀቅ አለ፡፡ ሐረግነት፡፡ በዲያስፖራ ማህበረሰብ የገንዘብ ፈሰስ ላይ ሀረግ ሆነው ህይወታቸውን የሚኖሩ ቤተሰቦች እና የመስራት አቅም ያላቸው ግለሰቦች ጥቂቶች ብቻ ናቸው ማለት አይቻልም፡፡ ሚዲያው አካባቢም ቢሆን (በመንግስትም ሆነ በግል) የሰከነ ምርመራ ቢደረግ “ሀረግነት” እና የ “ቤት አትክልትነት” ሊገኝ ይችላል፡፡
የ“ንጉሳቸውን” ወይም የ “ንግስታቸውን” ወይም የ “ጀግናቸውን” ወይም የ “ጎበዝ አለቃቸውን” ቃል ወይም ትዕዛዝ ወይም የይሁንታ ፊሽካ ድምጽ (ቡራኬ) አድምጠው “ተሰማራን” በሚሉበት መስክ የሚንቀሳቀሱ ሰዎች በኢትዮጵያ አሉ ብዬ አምናለሁ፡፡ በራስ መቆም እየቻሉ የህዝብ፣ የመንግስት፣ የተቋም፣ የድርጅት. . . ጥገኛ መሆን ተፈጥሮ የለገሰችንን ውስጣዊ እምቅ ኃይል ለማዳፈን ተሰማምቶ እንደመወሰን ሊቆጠር ይችላል፡፡ ሰዎችን ሀረግ አድርገው ለአላማቸው ማስፈፀሚያ ማንቀሳቀስ ወይም መማገድ የተካኑ መንግስታት፣ ተቋማትና ግለሰቦች እንዲሚኖሩም ማወቅ ብልህነት ነው፡፡ ይህንን ተገንዝቦ የሀረግ አስደጋፊዎች መጠቀሚያ ላለመሆን ቀድሞ መንቃትና እርምጃ ወስዶ መወሰን ተገቢነቱ አከራካሪ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም ሐረግነት ትክክለኛ ማንነትን አኮሳሽ እና አጥፊ ነውና፡፡
“ትግል እና ዕውቀት ከያ ትውልድ ጋር አላከተመም”
መስከረም 01 ቀን 2006 ዓ.ም በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ያነጋገርኩት ጋዜጠኛና የፖለቲካ ተንታኝ እስክንድር ነጋ በአገራችን በተለያዩ ዘርፎች እና ግለሰቦች ላይ ሀረግ የመሆን እውነታ መኖሩን ቢስማማበትም በኢትዮጵያዊ ትውልዶች ላይ ላለው የፈጠራ ክህሎት እና የታመቀ ኃይል የላቀ አፅንኦት ይሰጣል፡፡
ጋዜጠኛ እስክንድር ትውልዶችን ከጊዜ እና ከታሪክ አውድ አኳያ ታሪካዊ የጊዜ ፍሰታቸውን ጠብቆ ይተነትናል፡፡ ጊዜው ራቅ ቢልም፣ በአገራችን የነበረው አርበኝነት ራሱን የቻለ ጉልህ ታሪክ አሻራ ያሳረፈ የትውልድ ውጤት መሆኑንም ያስታውሳል፡፡ “ትግል እና ዕውቀት ከያ ትውልድ ጋር አላከተምም” በማለትም ከላይ የተጠቀሰው ትውልድ የራሱ የሆነ የፈጠራ ክህሎት እና የታመቀ ኃይል እንደነበረው አስረድቶ ነበር፡፡
በአፍሪካ የመጨረሻ የነበረው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ለአፍሪካም ሆነ ለዓለም ተምሳሌት መሆን የቻለ ትልቅ ታሪክ መስራቱን የሚናገረው እስክንድር ንቅናቄው ሁለት አብዮቶችን ማቀጣጠሉን ይናገራል፡፡ (ለአፄውና ለደርግ አገዛዝ መገርሰስ ምክንያት መሆናቸው ይገልፃል)በእስክንድር ዕይታ ኢህአዴግ ስልጣን ይዞ ነፃ ፕሬስን ካወጀ በኃላ በተፈጠረው ትውልድ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ታሪክ ለአፍሪካም ሆነ ለዓለም ደማቅ ገድል የሰራ መሆኑን በማስገንዘብ ለትውልዱ አክብሮቱን ገልፆል፡፡
“ድምፃችን ይሰማ” የተባለው ሠላማዊ የሃይማኖት ነፃነት ትግል ‹‹የዛሬ አዲስ ትውልድ›› በማለት የሚገልፀው ጋዜጠኛ እስክንድር ሰላማዊ በሆነ መንገድ ከፍተኛ የፈጠራ ክህሎቶቻቸውንና የታመቀ ኃይላቸውን እየተጠቀሙ መሆናቸውን በደስታ ይናገራል፡፡ ይህ ለአፍሪካ ሞዴል በመሆን በዓለም የታየ መሆኑንም ይመሰክራል፡፡
በኢትዮጵያ የቅርብ ጊዜ ታሪክ መሰረት የታሪክ ቅብብል ሆኖ ከተማሪዎች እንቅስቃሴ ወደ ጋዜጠኝነት፣ ከጋዜጠኝነቱ ደማቅ ታሪክ ወደ አክቲቪስትነት ትውልዳዊ ሽግግር ተያይዞ እየተከናወነ መሆኑን እስክንድር ያምናል፡፡
“በዓለም ላይ ደሴት የለም፤ ዓለም አንድ መንደር ሆናለች፡፡ ደሴት ለመሆን መሞከር የለብንም፡፡ በዓለም ላይ ብቻውን የቆመ ስልጣኔ የለም፡፡ ኢትዮጵያ እና ቻይና እራሳቸውን ከሌላው አለም ሲነጥሉ ነበር ቀደምት ስልጣኔያቸው የተዳከመው፡፡” የሚለው እስክንድር ከሌላው ዓለም ጋር መስተጋብር መፍጠር ጥንካሬ እንጂ ድክመት አለመሆኑን ይናገራል፡፡ ለዚህ ጽሁፍ መነሻ አላማም እንደማጠቃለያም ጥገኛ ሀረግ ሆነ ላለመገኘት እንደ ዜጋ እና እንደ አገር የራሳችንን እየፈጠርን ከውጭ አጣርተን ጠቃሚ የምንለው ስልጣኔ በመውሰድ ሁለቱንም አቀናጅተን መሄድ መፍትሄ መሆኑን እስክንድር ያስገነዝባል፡፡
የግል ልዑአላዊነት
እያንዳንዱ ሰው ሲፈጠር ጀምሮ የራሱ የሆነ ጥልቅ ማንነት ባለቤት ነው፡፡ ይህንን ማንነት መርምሮ በማወቅ በህይወት ዘመን ጥሪ ውጤታማ ሆኖ ለማለፍ ወሳኝ ቁርጠኝነት ከእያንዳንዱ ግለሰብ ያስፈልጋል፡፡ እግዜሩም በግለሰባዊ ማንነት በቅድሚያ ሲፈጥረን ይህ ልዩ ማንነት የላቀ ዋጋ እንዳለው ስለሚያውቅ ነው፡፡ አንዳችን ከአንዳችን የሚለየን ማንነት ለማንም ለጥቅም እና ለዝና የማንቀይረውና የማናስደፍረው፣ በሙያ መርህ የመቆም ሰብዕናችንን (Integrity) አሳልፈን የማንሰጠው መሆን ይገባዋል፡፡ በተፈጥሯዊ ማንነት ላይ ቆሞ ከሌሎች መሰል አባትና እናቶቻችን፣ እህትና ወንድሞቻችን ጋር ልዩነቶቻችን ተቀብለን ለተስማማንበት ዓላማ ህብረት ፈጥሮ መኖር ይችላል፡፡ ሉዓላዊ አገርን ሉዓላዊ ማንነት ባላቸው ግለሰቦች መገንባት ይቻላል፡፡
ራሱን መርምሮ ሐረግ መሆኑን የተገነዘበ ግለሰብ ወይም ተቋም ነቅቶ ወደ ትክክለኛ ጠንካራ የሜዳ አትክልት ማንነት መመለስ ይኖርበታል፡፡ ራስን፣ ቤተሰብን፣ ተቋምንና አገርን ለመታደግ ከሐረግ ማንነት መላቀቅ አንዱ መፍትሔ ነው፡፡ ሐረግ መሆን ካለብን ደግሞ ፈጣሪያችን ላይ መሆን ይገባዋል- አስተማማኝ ስለሆነ፡፡
አውቀውና ሳያውቁ ሐረግ የሚሆኑ እንዳሉ ሁሉ አውቀውና ሳያውቁ ሰዎችን ሐረግ የሚያደርጉም አሉ፡፡ ሐረግ በመሆን ውስጥ አልፈው የዱር አበባ የሆኑ እንዳሉ ሁሉ ሐረግ ሆነው ሌሌችንም ወደ ሐረግነት ጎራ የቀላቀሉም ይኖራሉ፡፡
በሐረግ ውስጥ ዋርካ (ጠንካራ) ማንነት አያብብም፡፡ በሐረግነት ውስጥ ግን ዋርካ የሆነ ማንነት አፈር ይበላዋል፡፡ ሌሎችን እያወቁ ወደ ሐረግነት ማንነት የሚያመጡ ብልጣብልጥ ሰዎች ያመጧቸውን ግለሰቦች አቅም፣ ችሎታ፣ ኃይልና ጊዜ ሲበዘብዙ ርህራሄ የላቸውም፡፡አውቀውም ሆነ ሳያውቁ ሐረግ መሆንና ሌሎችን ሐረግ ለማድረግ እሽቅድድም ለእምዬ አገራችንን ዋጋ ማስከፈሉ አልቀረም፡፡ ለሁለቱም ነቅተንና አንቅተን መፍትሄ ካላበጀልለት ረዥም ዓመታት በውድቀት መንገድ ማዝገማችን አይቀርም፡፡ የሐረግነት መብዛት ዋርካን አይፈጥርም፡፡
ፈጣሪ ሲፈጥረን በማንነታችን ዋርካ እንድንሆን ነው፡፡ ዋርካ እንጂ ሐረግ “ነበር” ተብሎ አይወሳም፡፡ መለስ ለኢህዴግ ዋርካ ነበር፡፡ እሱ ላይ የተንጠለሉ ግን እውነተኛ አስታዋሽ የላቸውም፡፡ መለስ ዋርካነቱን መቃብር ድረስ ይዞት ሄዷል፡፡ መቼም ቢሆን መስተዋሉና ጐልቶ መውጣት የሚችለው ዋርካ ብቻ ነው፡፡
የግል ስብዕና በሚገነባ ሥራ ተጠልለን ከእገሌ ወደ እገሊት አምልኮ ዥዋዥዌ መጫወት ቆም ብሎ ላሰበው ተገቢ አይደለም፡፡ ሐረግነት ትክክለኛ ስብዕና ያልጨበጠ አውራነት ይፈጥራል፡፡ ሐረግ የሆኑ “ተለጣፊ” የሚል ስያሜ የተሰጣቸው ፓርቲዎች በትክክለኛ ስብዕና ያልቆመ አውራ ፓርቲ ለመፍጠር አንድ ግብአት ሆነዋል፡፡ በሐረግነት የተገነባ አውራነት ደግሞ መጨረሻው ውራ ሆኖ መቅረቱ አይቀርም፡፡ ለዚህ ነው፣ አውራ ፓርቲ የሆነው ኢህአዴግ አንድ ቀን ውራ ሆኖ ስልጣኑ የሚያከትምለት፡፡ ሶሻሊስት አገራት ላይ ሐረግ የነበረው የደርግ ሥርዓት ተንኮታኩቶ ወድቆል፡፡ “ልማታዊ መንግስት” ብላ የአገሪቷን ነባራዊ ሁኔታ ሳያገናዝብ እነ ቻይና ደቡብ ኮሪያ እና ታይዋን ላይ ሐረግ ሆኖ አገር እየመራ የሚገኘው ኢህአዴግ ጊዜውን እየጠበቀ እንጂ መውደቁ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህ በ2006 ዓ.ም አውቀንም ይሁን ሳናውቅ ሐረግ ከመሆን ይሰውረን!

No comments:

Post a Comment