Thursday, September 26, 2013

አንድነቶች እና ፖሊሶች በጋራ ያሰሩት ወዳጄ

በመሐመድ ሐሰን


መቼም ርዕሱን ቀድማችሁ ያያችሁ ‹‹እንዴት ነው ነገሩ! ሲጀመር ኢትዮጵያ ውስጥ ፖሊስ ከተቃዋሚዎች ጋር መች ተባብሮ ያውቅና ነው?...›› አይነት ጥያቄ ትጠይቁ ይሆናል፡፡ እናንተ ልክ ናችሁ፤ የኔም ርዕስ ግን ትክክል ነው፡፡አንድነቶች እና ፖሊስ በጋራ ባደረጉት የየራሳቸው ርብርብ የልብ ወዳጄን አስረውታል፡፡ ‹‹እንዴታ?›› ካላችሁ ነገሩ እንደሚከተለው ይቀርባል፡፡
ሳንዶካን ደበበ የተባለው ወዳጄ ትላንት (መስከረም 14 ቀን 2006 ዓ.ም) እግሩ ዘወትር ከማይጠፋበት አራት ኪሎ ጥሎታል፡፡ ታዲያ ወዳጄ በተገኘበት አራት ኪሎ አንድነት ፓርቲ ለመስከረም 19 ለጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ቅስቀሳ እያደረገባቸው ካሉ አከባቢዎች አንዱ በመሆኑ ቅስቀሳቸውን አጧጡፈውታል፡፡ ይሄኔ በህዝብ አገልጋይነት ስም የኢህአዴግ አገልጋይ ሆነው የቀሩት የአራት ኪሎ ፖሊሶች፣ የአንድነት አባላትን እና የቅስቀሳ ቡድኑን ለማደናቀፍ እስከ መስከረም 19 መታገስ አልሆነላቸውም፡፡ ከቀስቃሾቹ የሚወጣው ድምጽም ሚያገለግሉትን ፓርቲ ክፉኛ ‹‹ያስቀይምብናል›› ብለው የሰጉም ይመስላሉ፤ ስለዚህ አላስቻላቸውምና ዘው ብለው የለበሱትን ልብስ በማይመጥን ፍጥነት እና አኳሀን ቅስቀሳውን አገቱት፡፡
በአከባቢውም ውዝግብ ተፈጠረ፤ መንገደኛውም ‹‹እንዴት ነው ነገሩ ፖሊስ እንዲህ ያለውን ተግባር መፈጸም አለበት እንዴ?›› ሲሉ ጠየቁ፤ ለራሳቸውም ‹‹ሼም! ነው!›› የሚል ምላሽ መስጠት ጀመሩ፡፡ ፖሊሶች ግን ‹‹መስሚያችን ድፍን ነው! ከኢህአዴግዬ ውጪ አይሰማንም፤ አናዳምጣችሁም!›› ያሉ ይመስላል የአንድነት አባላትን ሰብስበው ለእስር አዘጋጇቸው፡፡ ወደ እስር ቤት ከማምራታቸው በፊት ግን በዙሪያቸው ከተኮለኮለው አላፊ አግዳሚ ውስጥ የተወሰነውን ሰው ለአንድነቶች መመልመል ፈልገዋል፤ እነማን? አሳሪዎቹ- ፖሊሶች፡፡ ይሄኔ ነው ታዲያ ከጥግ ቆሞ ትዕይንቱ መስጦት በሞባይል ካሜራው ሲያስቀር የነበረው ወዳጄ በፖሊሶቹ የዓይን ካሜራ ውስጥ የገባውና በአባልነት የተመለመለው፡፡ እሱ በትዕይንቱ ሲመሰጥ እነሱ ደግሞ በሱ ቀድመው ተመስጠው ኖሮ ቀላቀሉት፡፡ ‹‹ምነው?!›› ቢል ማን ሊሰማው? ‹‹መስሚያ የለንም! አንድነት ነህ ብለናል አንድነት ነህ በቃ!›› ብለው ቀላቀሉት፡፡ ካሉ እኮ አሉ ነው፤ በዛ ላይ ደግሞ በእለቱ ሌላ ሰው በማሰር ሀራራቸው አልወጣላቸው ይሆናል፣ ቁጥሩን በርከት አድርገው ወደ እስር ቤት ይዘዋቸው ላፅ አሉ፡፡
የአንድነት ፓርቲ ቢሮ በየትኛው አቅጣጫ እንደሆነ እንኳን በውል የማያውቀው ጓዴ በፖሊሶቹ ምልመላ ለዕለቱ ሀያ ምናምን ደቂቃ አባል እንዲሆን ተገዷል፡፡ አዚህ አገር እኮ መሆንም አለመሆንም ችግር ነው፤ ሁሉም ነገር የሚወሰነው በነሱው ነው፤ ‹‹አሸባሪ፣ አክራሪ፣ ወዳጅ፣ጠላት፣ ኪራይ ሰብሳቢ፣ ሙሰኛ፣…›› እያሉ የሚፈርጁትስ በራሳቸው ተነሳሽነት አይደል! ወዳጄ ‹‹ኢትዮጵያዊ አይደለህም!›› ሊሉህ ሁሉ ይችሉ ነበር፤ ለመለስተኛው ደግነታቸው ምስጋና ማቅረብ ይገባሀል¡¡
እናላችሁ ይህ ቅጭጭ ያለው ወዳጄ (ታዲያ ልቧ ተራራ ነው፤ ዋ! ብዙ ካማረራችሁት ያው ነው…ሰው በስጋ፣ በሀብት፣ በጎሳ፣… አትመዝኑ፤) አብረውት በታፈሱ የአንድነት አባላት ከፍተኛ እና የተጠናከረ ርብርብ (እሱ እንደውም ተጠናከረ ሂበርተ ነው ያለው) ከነሱ ጋር እንዳልሆነ ለፖሊሶቹ ነግረዋቸው ሞባይሉ ከተፈተሸና ጉዳዩ ከተጣራ ቦሃላ ሊለቀቅ ችሏል፡፡
እዚህ ሀገር እስር ቀላልና በየትኛውም ሰዓት የፈለገው ነገር ጠለጥፎብን ልንታሰር የምንችልበት ድራማ ብዙዎቹ ሳይገባቸው አልቀረም፡፡ ከዚህ ወዳጄ የእስር ቤት ቆይታ ቦሃላ በ ‹‹ፌስ ቡክ›› ገጹ ላይ ብዙዎች ያሰፈሩት የስላቅ ምላሽም ይህንኑ ነው ያረጋገጠልኝ፡፡ እኔ ግን ሁኔታውን እንደነገረኝ ‹‹የሚጣራም የሚያጣራም በሌለበት ሀገር ላይ ይህቺን ታህል ደቂቃ ብቻ ታስረህ መፈታትህ እድለኝነትህን ያሳያልና በፍጥነት ሎተሪ ሞክር፡፡›› ነበር ያልኩት፡፡ እውነቴን እኮ ነው የፈለጉትን ነገር ሊሉት ይችሉ ነበር፤ መረጃ ቢያጡ እንኳን ፣‹‹ወደፊት አሸባሪ መሆኑ ስለማይቀር ከወዲሁ በቁጥጥር ስር አውለነዋል፤›› ብለው ለዛ ማነው ኢቴቪ ውስጥ ቁጭ ብሎ ፊልም የሚቆራርጠው? አዎ! ለሱ ሰጥተው ዶክመንተሪ ሊሰሩብህ ይችሉ ነበር፡፡
በመጨረሻ ላይ ያካፈለኝ ሀሳብ ግን ለኔ በጣም ወሳኝ መስሎ ታይቶኛል፡፡ ቃል በቃል ያለኝን ሳሰፍረው ‹‹… እኔ ግን አንድነቶች በፍቅራቸው አስቀንተውኝ፣ በአንድነታቸው አስረውኝ፣ ከእስር ቤት አስፈትተውኛል፤›› የሚል ነው፡፡ ከዚህ አባባል ውስጥ ወዳጄ በፖሊሶች የተሳሳተ ድርጊት አማካይነት ለአንድነቶች ሁለቴ መመልመሉን እንመለከታለን፡፡ በመጀመሪያ በስህተት ቦሃላ ግን ለማያውቀው ነገር በማጋለጥ፡፡ እኔ ግን አሁንም ይበልጥ ማስረገጥ የምፈልገው ‹‹…አንድነቶች በፍቅራቸው አስቀንተውኝ፣ በአንድነታቸው አስረውኝ፤…›› ሲል የገለጻት ነጥብ ላይ ነው፡፡ ወዳጄ ለምስክርነት ያስቀመጣት ነገር የምር ሙሉ ለሙሉ በፓርቲው ውስጥ የሚታይ ከሆነ እሰየው ነው፤ ተጠናክሮ መቀጠል ያለበትም እንዲህ ለምስክርነት የሚበቃው እንደስማቸው አንድነታቸው እና ፍቅራቸው ነው፡፡ የምር ሀገር የምትለወጠውም በሁሉም ፓርቲ ውስጥ ወዳጄ የገለጸው አንደነት እና ፍቅር ሲኖር ነው፤ አለበለዚያ ግን ‹‹ሁሉም ነገር ከንቱ ነው! የከንቱ ከንቱ…›› ወዳጄ አንተው ጨርሰው፡፡
በመጨረሻ ግን በወቅቱ እስር ቤት ለነበራችሁት እና ወዳጄ ምስክርነቱን የሰጠላችሁ እንዲሁም ወዳጄን በፍቅራችሁ እና አንድነታችሁ ላሰራችሁት የአንድነት አባላት ትክክለኛውን ነገር ስለያዛችሁት ቪቫ! ብያለው፡፡
የመጨረሻ መጨረሻ ህሊናዬ እንዲህ ሲል ሞገተኝ ‹‹ አንድነት እና ፍቅር የሚጠነክረው በእስር ግዜ ብቻ ይሆን እንዴ?›› እኔ እንጃ እያሰላሰልኩት ነው፡፡ እናንተ ግን መልስ ካላችሁ ወዲህ በሉን፡፡    

No comments:

Post a Comment