Tuesday, August 20, 2013

ከመለስ በፊት ሌላ መለስ የሚባል ነበር ?

በሀገራችን ታሪክ ተመሳሳይ ስም ያላቸው ነገስታት ይገኛሉ ለምሳሌ ዮሐንስ የሚባሉ አራት ነገስታት ነበሩ እነሱን ለመለየትም ዮሐንስ አንደኛ፣ ዮሐንስ ሁለተኛ ዮሐንስ ሶስተኛ እና ዮሐንስ አራተኛ ይባላሉ :: ስለዚህ አንድ ሰው ዮሐንስ ስለሚባል ንጉስ ቢሰማና የሚሰማዉ ነገር እሱ ከሚያውቀው ዮሐንስ ባህሪ እና ታሪክ የተለየ ከሆነ ምን አልባትም እየተወራ ያለው ስለሌላኛዉ ዮሐንስ ስለሚሆን የትኛዉ ዮሐንስ ብሎ መጠየቅ አለበት::

እኔም ሰሞኑን ኢቲቪን ስመለከት ስለመለስ የማየዉ እና የምሰማዉ ነገር ፈፅሞ ከማውቀው መለስ የተለየ ሁኖብኛል፤ ጣት ቆራጩ መለስ፣ ታዳጊወችን እና ነፁሃንን ስለተቃወሙት በአደባባይ ገድሎ ባንክ ሲዘርፉ ተገደሉ የሚለውን መለስ፣ የህዝብ ድምፅ የሚዘርፈውን መለስ የይስሙላ ምርጫ እያደረገ በህዝብ የሚያላግጠውን መለስ የትምህት ጥራትን ከዜሮ በታች ያወረደውን መለስ የኢህአዴግ አባል ሳይሆኑ ሥራና የትምህርት ዕድል ወዘተ ማግኘት እና በሀገር ላይ በሰላም በነፃነት ያለፖለቲካዊ ተፅእኖ የፈለጉትን ሥራ እየሰሩ የመኖር መብትን የሚነገፈዉን መለስ፣ ህዝብን በዘር ለያይቶ እርስ በእርሱ በጠላትነት እንዲተያይ ያደረገዉን መለስ ህዝን በኑሮ ዉድነት መከራ ያሳየዉን መለስ …. አረ ሰንቱን ማለት ይቻላል::ስለመለስ ከእኛ በሱ ዘመን ከኖርን ኢትዮጵያዉያን በላይ ማን ሊያውቀው ይችላል? ምን አልባት ከመለስ በፊት ሌላ መለስ የሚባል ኢትዮጵያን ያስተዳደረ መሪ ነበር ወይ ? ኢቲቪ የሚያወራውም ስለሱ መሆን አለበት:: ክፉ አናጋሪው ኢቲቪ ከፌስ ቡክ ለተወሰነ ጊዜ ገለል የማለት ዉሳኔን አስቀየረህ ክፉ አናገርከኝ፣ ክፉ አናጋሪ!
Mastewal Dessalew


No comments:

Post a Comment