Sunday, April 7, 2013

የጋዜጠኛ እስክንድርና የእነ አንዷለም አራጌ ይግባኝ እልባት አላገኘም


የጋዜጠኛ ተመስገን ጠበቃ ተጨማሪ ጊዜ ጠየቁ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት፣ በሽብርተኝነት ከተፈረጁ ድርጅቶችና ሽብር ለመፈፀም ከሚፈልጉ ሰዎች ጋር ሰርታችኋል በሚል ተከሰው የተፈረደባቸው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እንዲሁም የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ የነበሩት የእነ አንዷለም አራጌ፣ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ያቀረቡት የይግባኝ አቤቱታ በረቡዕ እለቱ ቀጠሮ እልባት ሳያገኝ ተላለፈ፡፡ በእለቱ በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የችሎት አዳራሽ ውስጥ የታሳሪ ቤተሰቦች፣ የአገር ውስጥና የውጭ ጋዜጠኞች እንዲሁም ሌሎች ሰዎች ችሎቱን ለመከታተል ቦታውን ሞልተው የዳኞችንና የታሳሪዎችን መምጣት እየተጠባበቁ ነበር፡፡ ቢጠባበቁም ግን አልተሳካም፡፡

በመጨረሻ የእነ አንዷለም ጠበቆችና አቃቤ ሕጉ ወደ ጽ/ቤት ተጠርተው ሲሄዱ ነው፤ ምን እንደተፈጠረ ለማወቅ የተወሰኑ ጋዜጠኞችና የታሳሪ ቤተሰቦች ተከትለዋቸው የሄዱት፡፡ የመሀል ዳኛው አቶ ዳኜ መላኩ፣ ለታሳሪ ጠበቆችና ለአቃቤ ህግ ባቀረቡት ማብራሪያ፣ በዚሁ መዝገብ 30 ያህል ሰዎች ይግባኝ የጠየቁ መሆናቸውን፣ መዝገቡም ለ10 ቀን ዘግይቶ እንደደረሳቸው ጠቅሰዋል፡፡ “መዝገቡ ሰፊ ነው፤ ጉዳዩን ረጋ ብለንና ሰፊ ጊዜ ወስደን ልንመረምረው ይገባል” በማለት የተናገሩት የመሃል ዳኛው፤ ለመጋቢት 30 ቀን 2005 ተለዋጭ ቀጠሮ እንደሰጡ ገልፀዋል፡፡ ዳኛው ከዚህም በተጨማሪ፣ ማረሚያ ቤቱ ለምን እስረኞቹን ወደ ፍ/ቤት አላቀረበም በሚል ለማረሚያ ቤቱ ተወካይ ጥያቄ ያቀረቡ ሲሆን፣ የቀጠሮ ትዕዛዝ አልደረሰንም የሚል ምላሽ አግኝተዋል፡፡
ዳኛው ግን፣ “በእኛና በማረሚያ ቤቱ ፀሐፊዎች መካከል መካካድ ተጀምሯል ማለት ነው እኛ ቀጠሮውን በወቅቱ ለማረሚያ ቤቱ ፀሐፊዎች ሰጥተናል” ብለዋል፡፡ የማረሚያ ቤቱ ተወካይ በእለቱም በጠቅላይ ፍ/ቤት የተገኙት ሌላ ተለዋጭ ቀጠሮ ለመውሰድ እንደሆነ ለዳኛው አስረድተዋል፡፡ በሌላ በኩል፤ የወጣቶችን ሀሳብ በማናወጥ፣ ለአመፅ በማነሳሳትና የመንግሥትን ስም ማጥፋት በሚል ክስ የቀረበበትን ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን በመወከል ጠበቃው ለከፍተኛ ፍ/ቤት ባቀረቡት ጥያቄ፤ ምስክሮችን ለማደራጀት ተጨማሪ ጊዜ እንደሚያስፈልጋቸው ገልፀው፣ ለሚያዚያ 15 ቀን 2005 ዓ.ም መከላከያ ምስክሮች እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

No comments:

Post a Comment