Wednesday, April 10, 2013

የባለራእዩ ራእይ መግቢያ፣

የአማራ ብሔር ተወላጅ የሆኑ ዜጎች ከመኖሪያቸው የመፈናቀላቸው አሳዛኝ ዜና፣ ዜና ብቻ ሆኖ የሚቀር የሚመስለው ይኖር ይሆናል። ተፈናቃዮቹን የሚያጽናና ተአምር ተፈጥሮ ነገሩ ዜና ብቻ ሆኖ ቢቀር እኔም በወደድኩ። ነገር ግን እውነቱ እርሱ አይደለም። ተፈናቃይና አፈናቃይ በግለሰብ፣ ቢበዛም በፖለቲካ ቡድን (ርእዮተ ዓለም) ደረጃ የሚለያዩ ሲሆን ጊዜያዊ ጉዳቱ ባይቀንስም ዘላቂ ጣጣው ግን ቀላል ነው። ላለፉት ዓመታት የሰማነው፣ አሁንም የምንሰማው ግን ተፈናቃዩ፣ ታሳሪው፣ ተሳዳጁ ዜጋ የሚገለጸው የሆነ ብሔር ተወላጅ ተብሎ ነው። ተፈናቃይ ብሔር አለ። አፈናቃዩ ማነው? አፈናቃዩ ግለሰብ ነው፣ ፖለቲካዊ ቡድን ወይስ ሌላ ብሔር? የዛሬው ተፈናቃይ ብሔር፣ የዛሬው አፈናቃይ ብሔር...አሉ ማለት ነው? በአገራችን ብሔረሰቦች መካከል የነበረው የባህልና የፖለቲካ ቁርሾ ጥንትም የነበረ ነው።
እንዲህ በአጭሩም ይፈታል ብሎ የሚቃዥ የለም። ነገር ግን የአሁኑ ባሰ። ያለፈው አመት በቂ ትምህርት ሳይሆን ቀርቶ ነው በአዲስ ዙር ማፈናቀሉ አያያዙ እንኳን ሳይለወጥ የሚደገመው? አፈናቃዮቹ ከወረዳቸው ውጭ የሚኖር ዘመድ የላቸውም? ይሔ የብሔር መመዘኛ ያዋጣል? ቦታቸው ተወሰደባቸው ለተባሉት ሕዝቦች/ብሔረሰቦችስ ቢሆን በአሁኑ ማፈናቀል ለዘለቄታው ይጠቅማል? የነገው ተፈናቃይ ማን እንደሚሆን የሚወስነው የዛሬው አያያዛችን አይደለምን? ኢትዮጵያ የምትባል አገር እንደነበረችና አሁንም እንዳለች፣ ይቺ አገር ከበቂ በላይ ችግር እንዳለባት፣ ለመተንተን የሚቸግር ከብሔረሰብ ጋራ የተያያዘ ውስብስብ ሸክም እንዳለባት ረስተውታል? 

"ወገኔ፣ የአገሬ ልጅ" ማለት ቢቀር "ነግ በእኔ" ማለት እንደምን ተረሳ? ሰዎቹ "በሕገ ወጥ መንገድ ሰፍረዋል" ቢባል እንኳን፣ እነርሱን በግፍና በገፍ ማፈናቀል ከሚያስከትለው ዘላቂ አደጋ አንጻር "ለኢንቨስተሩ" ሌላ ቦታ ተፈልጎ ጠፍቶ ነው? ወይስ ኢንቨስትመንቱ የብሔረሰብ ጥላቻና ቂም የማምረት ኢንቨስትመንት ነው? "ኢንቨስትመንት" ስትሉ...።

ብዙዎቻችሁ ስለሟቹ መለስ የኢተርሀሙዌ ትንቢት ታስታውሳላችሁ። እርሱ በሰጣቸው መመሪያ ነገሩን ወደ አደዳባባይ ያመጡትን ግኡዛን ጀሌዎች እርሷቸው። ታዲያ በአንድ ጽሑፍ መለስ ስለኢነተርሐሙዌ ካነሳ አይቀር የእኛዎቹን ሁቶዎችና ቱትሲዎች ገልጦ እንዲነግረን ጠይቄ ነበር። ለነገሩ ሁሉም በቤቱ የሚያወራው ነው። ጨፍጫፊና ተጨፍጫፊ በሌለበት ጭፍጨፋ አይኖርም። ታዲያ አሁን የምናየው ስለባራእዩ ራእይ ምን ይነግረናል?

ኦ ኢትዮጵያ! ታዳጊሽ ወዴት አለ?! መንግሥትሽ ያንቺ አይደለምና የዛሬ ሕመምሽ፣ የነገ መከራሽ አይገደውም። አምላክ ያለሽ አይመስለኝም፤ ካለሽም ትቶሻል፤ እመኚኝ ፍቅሩን ለሌላ ሰጥቶብሻል። እግዜርሽ ሕዝብሽ ነበር። ሕዝብሽም ገና ከግፍ እስራቱ አልተፈታም። የሚሞቱልሽ፣ የሚታሰሩልሽ ልጆችሽ መስዋእትነት መና እንዳይቀር አውቃለሁ።
ተስፋሽ ታድጎኛል።

የዛሬ አፈናቃዮች በብሔረሰብ ካባ ለመደበቅ ቢሞክሩም ሕግ ፊት የሚቀርቡበት ቀን እንደሚመጣ አምናለሁ። ተፈናቃዮዩቹ በሙሉ የአማራ ብሔር ተወላጆች ቢሆኑም አፈናቃዩ ወገን ግን የየትኛውም ብሔር ወኪል እንዳልሆነ እናስታውስ፤ አደራ። ግፈኞቹ፣ መዝባሪዎቹ፣ ወሮበሎቹ፣ ሆድ አደሮቹና ዘረኞቹ አፈናቃዮች ብሔራቸው "ነውር" ነው። ነውረኞች።

No comments:

Post a Comment